Monday, May 7, 2012

የአዳም እናትነት



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
29/08/2004
አምላኬ ሆይ አንተ ስለኢየሩሳሌም ጥፋት አዝነህ “ኢየሩሳሌም ኢየሩሳሌም ሆይ ነቢያትን የምትገድል ወደ እርሷ የተላኩትንም የምትወግር ዶሮ ጫጩቶቹዋን ከክንፎቹዋ በታች እንደምትሰበስብ ልጆችሽን እሰበስብ ዘንድ ስንት ጊዜ ወደድሁ አልወደዳችሁምም”(ማቴ.23፡37) ብለህ በተናገርከው ኃይለ ቃል   የአዳምን እናትነት ልብ አልኩኝ፡፡
ጌታችን አዳምን ከምድር አፈር አበጅቶ የሕይወት አስትንፋስን እፍ አለበት፤ በዚህም ምክንያት አምላኩን መሰለ፡፡ ከጎኑም አንዲት አጥንትን ወስዶ በእርሱ አርአያና አምሳል ሔዋንን በማበጀት በአካል እንድትገለጥ አደረጋት፡፡ ከዚህም በኋላ ከእነርሱ የሚገኙ ሁሉ እነርሱን እንዲመስሉ እነርሱ ያላቸውን ሕይወት ሕይወታቸው አድርገው እንዲኖሩ በእነርሱና በዘሮቻቸው የልጅ ልጆቻቸውን ሁሉ ፈጠረ፡፡ እንዲህ በመሆኑም የአዳም ቅድስና ለእነርሱ ሕያውነት፤ የእርሱ ውድቀት ለእነርሱ ውድቀት ሆነ እንጂ ልክ እንደ መላእክት አንዱ ቢወድቅ ሌላው ጸንቶ በመቆም የሚድን አልሆነም፡፡ ስለዚህም አዳም ወደቀ እኛም የእርሱ የውድቀቱ ተጋሪዎች ሆንን፡፡ እግዚአብሔር በረድኤት ከአዳም ሲለይ ከእኛም በረድኤት ተለየ፡፡ ምንም እንኳ የአዳምና የሔዋን ኃጢአት ተባባሪዎች ባንሆንም የውድቀታቸው ተጋሪዎች ሆንን፡፡ ምክንያቱም በአዳም አንድ ሰው ሆነን ተፈጥረናልና፡፡

አሁን ግን ይክበር ይመስገንና ፍጹም ንጹሕና ቅዱስ ከሆነው ዳግማዊው አዳም ከተባለው ክርስቶስ ልክ እንደ ሔዋን አዳም አባታችንንም ጨምሮ በአዲስ ተፈጥሮ ተፈጠርን፤ በእርሱም ሕያዋን ተባልን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ "አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም ባሪያም ጨዋ ሰው የለም ወንድም ሴትም የለም ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁ" እንዲል በእርሱ አንድ ሰው ሆነናል፡፡(ገላ.3፡27-28) ነገር ግን የአዲሱ ተፈጥሮአችን መገኛ ግንዱ ከሆነው ከክርስቶስ ስንለይና እርሱን ሳንመስል ስንቀር ከእርሱ እንቆረጣለን፤ እንደ ጭራሮም ተለቅመን ወደ እሳት እንጣላለን፤ ይህ ደግሞ እጅግ የሚያስደነግጥ ነው፡፡
ፍቅሩ እኛን አካሉ እስከማድረግ ደርሶ እጅግ ታላቅ እንደሆነ እንዲሁ ጭካኔውም አካሉ ከመሆን እኛን ቆርጦ ለእሳት እስከ መስጠት የሚደርስ እጅግ ብርቱ ነው፡፡ የጌታችን ጭካኔ ግን ከእርሱ የመነጨ አይደለም፡፡ የራስን አካል ቆርጦ መጣል እንዴት የሚያስጨንቅ ነገር ነው!!! ቅዱስ ጳውሎስ  “ማንም የገዛ ሥጋውን የሚጠላ የለም ነገር ግን የአካሉ ሕዋሳት ስለሆንን ክርስቶስ ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን እንዳደረገላት ይመግበዋል ይንከባከበዋል”(ኤፌ.5፡30)ብሎ እንደመሰከረው እርሱ እኛን ፈጽሞ አይጠላንም፡፡ ፍቺም እንዲሁ አካልን ቆርጦ እንደመጣል እጅግ ከባድ ነው፡፡ ነገር ግን እኛ ከእርሱ ጋር መኖርን ሳንፈቅድ ስንቀር በግድ ተጭኖን እንድንቀጥል አያደርገንም፤ እንዲህ ማድረጉ ችሎታው ስለሌለው ሳይሆን ፈቃዳችንን ስለሚያከብርልን ብቻ ነው፡፡ ቢሆንም የእርሱ ናፍቆት የእኛ መዳን ነውና ስለዚህም እጅግ ይታገሰናል፡፡ ነገር ግን እርሱን ክደን ከሌላ ጋር ስናመዝር ፍቺው ያኔ ይፈጸማል፡፡ ያም ማለት ተቆርጠን እንጣላለን፡፡ ይህ ደግሞ እጅግ የሚያስፈራ ነው፡፡ የሚደንቀው ግን እግዚአብሔርን እኩል ማፍቀራችንና መፍራታችን ነው፡፡ ስናፈቅረው እርሱን መፍራታችን እንዳለ ሆኖ ነው፤ ስንፈራውም እርሱን ማፍቀራችን እንዳለ ሆኖ ነው፡፡ እርሱም ለእኛ አባትም አምላክም ነው፡፡ እንደ አባትነቱ እናፈቅረዋለን እንደ አምላክነቱ እንፈራዋለን፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከእርሱ እንዳንቆረጥ እርሱን ልንፈራው ግድ ነው፡፡ አካሉ አድርጎ እንዲህ ስለወደደን ደግሞ እናፈቅረዋለን፡፡ ስለሆንም በጽድቅ ሕይወት መትጋታችን እርሱን ስለምናፈቅረውና ስለምንፈራው ይሆናል ማለት ነው፡፡
 እናት ከአካሉዋ ተከፈሎ በጭንቅና በጋር የወለደችውን ልጇን ምንም በኃጢአት ሕይወት ውስጥ ቢሆን እንደምትወድና ስለእርሱ እንደምትጨነቅ እንዲሁ ጌታችን ስለእኛ ጭንቅ የሆነ መከራን ተቀብሎ ከጎኑ፤ ከልቡ አጠገብ እኛን ወልዶናልና ከእናትም በላይ  ይወደናል፤ ስለዚህም ስለእኛ  ኃጢአት ሳይሆን ስለእኛ መመለስ ይጨነቃል፡፡ ነገር ግን እኛም ልክ እንደ ኢየሩሳሌም በክንፎቹ ሊሰበስበን ሽቶ በወንጌል ሲጠራን ከክንፎቹ ውስጥ ልንሸጎጥ ባንወድድ ነጣቂው አሞራ ሰይጣን እኛን ነጥቆ ባጭር ያስቀረናል፡፡ በጥፋታችን ግን ጌታችን “ዶሮ ጫጩቶቹዋን እንደምትሰበስብ ልጆችሽን እሰበስብ ዘንድ ስንት ጊዜ ወደድሁ አልወደዳችሁምም” እንዳለው እጅግ ያዝናል እንጂ አይደሰትም፡፡ እንዴት እናት የልጁዋ ጥፋት ሊያስደስታት ይችላል? ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ ከእናትም በላይ ነው፤ ስለዚህ ስለኢየሩሳሌም መጥፋት እንዳነባ ስለእኛም ጥፋት እጅግ ያዝናል ምክንያቱም ከሥጋው ሥጋ ከአጥንቱ አጥንት የሆንን ልጆቹ ነንና፡፡  
 አምላካችን ሆይ በእቅፎችህ ውስጥ ሆነን ልክ እንደ ሕፃናት ንጹሐንና ቅዱሳን ሆነን በደኅንነት የተወደደ መዓዛ ያለውን ጠረንህን እያሸተትንና ሙቀተ መንፈስ ቅዱስን እየሞቅን ብርቱዎች እንድንሆን ይህን መረዳትን ስጠን፤ አንተም ከምትሰጠን የሕይወት ምግብ ተመግበን በአካልም በአእምሮም በማደግ አንተን እንድንመስልህና ልጆችንም ወልደን በቃልህ ወተትነት እንድናሳድጋቸው የምትወደን አምላካችን ሆይ ፈቃዳችን ለፈቃድህ የሚያደላ እንዲሆን ፍቅርህን ለእኛ በማሳየት እርዳን፡፡ ፍቅርህን እንድናስተውለውም ዐይነ ልቡናችንን አብራልን፡፡  ጌታ ሆይ እኛ የሥጋ ፈቃዳችንን መግዛት ተስኖናል፤ ልባችን ፈቃድህን ቢያውቅም ለኃጢአት ፈቃድ ተገዝቶአል፡፡ አምላክ ሆይ እባክህ እርዳን ዝም አትበለን፤ የፈቃድህን ጣዕም አቅምሰን ኃጢአትንም እንድንጸየፋትም እርዳን፡፡ አንተ ከእናትም በላይ ርኅሩኅና መሐሪ ነህና ራራልን ይቅርም በለን፡፡
አምላኬ ሆይ አንተ ለእኛ እናታችን እንደሆንክ አዳምም ለሔዋን እናቱዋ መሆኑን አሁን ተማርኩ፡፡ እናትነትንም ለሔዋን ያስተማራት እርሱ አዳም እንደሆነም ተረዳሁ፡፡ ስለዚህ እኛ አዳማውያን ራሳችንን በአዳም ቦታ አስቀምጠን ለፍቅረኞቻችን፣ ለእጮኞቻችን፣ ለሚስቶቻችን እናትነትን የማስተማር ግዴታ እንዳለብንም እንወቅ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም “ሴት ልጅ በነገር ሁሉ እየተገዛች በዝግታ ትማር ሴት ግን በዝግታ ትኑር እንጂ ልታስተምር ወይም በወንድ ላይ ልትሠለጥን አልፈቅድም፡፡ አዳም ቀድሞ ተፈጥሮአልና በኋላም ሔዋን ተፈጠረች”ማለቱ ለዚህ ነው፡፡ ወንድ ክርስቶስን መስሎ ልጆችን በእውቀትን በማስተዋል እንድታሳድግ ለሚስቱ ሊያስተምር ይገባዋል፡፡ እርሱዋም ልጆቹዋን ተፈጥሮአዊ በሆነው እናትነት ጠባዩዋ ብቻ ሳይሆን ከባልዋ ባገኘችው መንፈሳዊ እውቀትና ማስተዋል ልታሳድጋቸው ይገባታል፡፡ እንዲያ ሲሆን “በእምነትና በፍቅር በቅድስናም ራሳቸውን እየገዙ ቢኖሩ በመውለድ ትድናለች”(1ጢሞ.2፡11-15) የሚለው ቃል በምላት ይፈጸምላታል፡፡
ግን ግን እኛ አዳማውያን ለሚስቶቻችን የምናካፍለውን እናትነትን በእርግጥ እናውቀዋለንን? እኔ ግን ጥርጣሬ አለኝ፡፡ አይደለም ይህንን እናት ስለመሆናችን እንኳ ብዙዎቻችን የምናቅ አይመስለኝም፡፡ ስለዚህም ልጆቻችን እንደ እንስሳት አድገው እንደ እንስሳት ኖረው እንደ እንስሳት ይጠፋሉ፡፡ ይህ እጅግ የሚያሳዝን ነው፡፡ ብዙዎቻችን በዚህ መልክ አደግን ሰውነታችን ኃጢአትን ለምዶ ከዚህ ክፉ ልማድ ለመውጣት ተሳነን፡፡ ለዚህ ሁሉ ጥፋት ተጠያቂዎቹ እኛው አዳማውያን ነን፤ ምክንያቱም እኛ አስቀድመን ክርስቶስን አልመሰልነውምና፤ ክርስቶስን መምሰልንም ለሚስቶቻችንን አላስተማርናቸውምና፡፡ ክርስቶስ ለእኛ እናታችን ሆኖ የወንዶች እናትነትን ገለጠው፡፡ እኛ ግን ፈጽሞ ዘነጋነው፡፡ ይህ ግን እንዳይደገም አዳም ወገኔ ሆይ እናት መሆንህም አትዘንጋ የክርስቶስንም እናትነት ገንዘብህ ለማድረግ ትጋ፡፡ ኦ አምላካችን ሆይ የአንተን እናትነት ገንዘባችን እናደርግ ዘንድ እርዳን፡፡ ፍቅር ለሆንከው ለአንተ ክብር ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን!!!           

1 comment:

  1. kale hiwot yasemaln tsegawn yabzalh ya agelglot edmihn yibarklh edmina tina yisteh amlake kudusan.... AMEN....

    ReplyDelete