Sunday, February 26, 2012

"ሕይወትም ቢሆን ሞትም ቢሆን..."


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
19/06/2004
እግዚአብሔር አምላካችን የፍጥረት ቁንጮ የሆነውን እኛን በሞትና በሕይወት ምሳሌ ፈጠረን፡፡ አዳምን በሞት ሔዋንን ደግሞ በሕይወት ምሳሌ ፈጠራት፡፡ እኛ ዘር እንሰጥና እሩጫችንን ስናበቃ ሴት ልጅ ግን በአካልዋ ውስጥ ለሰጠናት ዘር ሕይወትን በመስጠት ሕይወትን ትቀጥላታለች፡፡ እኛ ወንዶች ከሴቶች ይልቅ ሞትን ማሰብ በውስጣችን ስላለ የልጆቻችን ቀጣይ ሕይወት ሲያሳስበን ሴትን ልጅ ግን ሕይወት በእጁዋ ስለሆነ  ዕለታዊው የሆነው ነገር ያስጨንቃታል፡፡
 እኛ ወንዶች ዘርን ሰጥተን በሕሊናችን ይህችን ዓለም አሳልፈናት ስንሰናበታት፤ ሴት ልጅ ግን ለዚህች ዓለም ሕይወትን ሰጥታ ሕያዋን ልጆችን በመውለድ ዳግም እኛን በልጆቻችን ሕያዋን በማድረግ ሕይወትን እንድንኖራት ታደርገናለች፡፡ እኛ ሞትን አስበን ራእይን ለልጆቻችን ስናሰንቃቸው፤ ሴት ልጅ ግን ሞት በእርስዋ ውስጥ አይታሰብምና ለእነርሱ በሕይወት መቆየት ትታትራለች፡፡
ሞትና ሕይወት ፈጽመው የሚጣጣሙ ባይሆኑም እግዚአብሔር አምላክ አጣጥሞ ያውም በእኛ ተፈጥሮ ውስጥ ገለጣቸው፡፡ አዳም በሞት አርአያ አንቀላፍቶ ሳለ ሔዋንን አስገኛት፡፡ እርሱዋም ምድሪቱን ከእርሱ ባገኘችው ዘር በሕይወት ሞላቻት፡፡ ክርስቶስ ኢየሱስም በሞቱ ቤተ ክርስቲያንን መሠረታት፤ እርሱዋም ከእርሱ ባገኘችው ዘር መንፈስ ቅዱስ ምድርን በሕያዋን ልጆቿ ከደነቻት፡፡
ጌታችን የሞት ምሳሌ የሆነውን የአዳምን ተፈጥሮ በሞቱ ሲያከብረው የሕይወት ምሳሌ የሆነውን የሴትን ተፈጥሮ ደግሞ በትንሣኤው አከበረው፡፡ ስለዚህም ለእኛ ለክርስቲያኖች ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው በዚህ ምድር መኖራችን  ጥቅም ነው፤ ከዚህ ዓለም ተለይተን ከክርስቶስ ጋር መኖርም ለእኛ እጅግ መልካም ነው፡፡(ፊል.1፡23-24) ለዚህም ይሆናል ይህ ሐዋርያ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች “ሁሉ የእናንተ ነው” ካለ በኋላ “… ዓለምም ቢሆን ሕይወትም ቢሆን ሞትም ቢሆን ያለውም ቢሆን የሚመጣውም ቢሆን ሁሉ የእናንተ ነው እናንተም የክርስቶስ ናችሁ ክርስቶስም የእግዚአብሔር ነው”ማለቱ፡፡(1ቆሮ.3፡22-23)ድንቅ ነው!!!  

No comments:

Post a Comment