Thursday, February 9, 2012

“አንዲት አጥንት”



ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
01/06/2004
ከዛሬ ስድስት ዓመት በፊት የተጻፈ 


 “ከአዳም የጎን አጥንት የተፈጠረችው ሴት ከራስ ቅሉ አጥንት አለመፈጠርዋ በእርሱ ላይ እንዳትሰለጥን ነው ከእግሩም አጥንት ከአንዱ አለመፈጠሯ እርሷን መበደልም ይሁን መጨቆን እንዳይገባው ለማስተማር ነው፡፡ ነገር ግን ከጎን አጥንቱ ፈጠራት በክብር እኩል መሆናቸውን ለማሳየት፡፡ ይህ የጎን አጥንት ከክርኑ አካባቢ መሆኑ ሚስቱን ከጥቃት ሁሉ ይጠብቃት ዘንድ የባል ሚና መሆኑን ለማስገንዘብ ነው፡፡ እንዲሁም ከልቡም አጠገብ መፈጠሩዋ እርሷን ከልቡ ሊያፈቅራት እንዲገባው ለማመልከት ነው፡፡”(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቅዱስ ያዕቆብ ዘስሩግ)
ቅዱሳን እንዳስተማሩን እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ማዕከላዊ አድርጎ መፍጠሩ በዐይን የማይታዩትን መናፍስትንና የሚታዩ ፍጥረታትን ሁሉ እርሱ እንደፈጠረና ግዢያቸው እንደሆነ ምስክር እንዲሆነው ነው ይላሉ፡፡ ባጠቃላይ ሰው /Human beings/ የእግዚአብሔር የገዢነቱ ምልክት ነው፡፡
ስለዚህም አዳም በነፍስ ተፈጥሮው መልአካዊ ባሕርይ ሲኖርው በሥጋው ባሕርይው ደግሞ እንስሳዊ ባሕርይ ይንጸባረቅበታል፡፡ በዚህም መሠረት አዳም በሥጋው ባሕርይው ምክንያት ልክ እንደ እንስሳት ለመኖር መሠረታዊና አስፈላጊ ነገሮች የተባሉት ሁሉ ለእርሱ የተገቡ ሆኑ፡፡

መላእክት ረቂቃን፣ አዋቂዎች፣ ሕያዋንና ነፃ ፈቃድ የተሰጣቸው ፍጥረታት ሲሆኑ በዚህም ተፈጥሮአቸው እግዚአብሔር አምላካቸውን ይመስሉታል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር አምላካችን በባሕርይው ረቂቅ፣ ሕያው፣ የፈቃዱን የሚፈጽም አምላክ ነውና፡፡ ቢሆንም ሰው ከመላእክት ይልቅ እግዚአብሔርን ይመስለዋል፡፡ ረቂቋ ነፍስ ሥጋን ተዋሕዳ ለሥጋ ሕይወትን እንደሰጠች እንዲሁ ረቂቁ እግዚአብሔር በፍጥረታት ሁሉ ሕልው በመሆን ከእርሱ በተገኘች ሕይወት ያኖራቸዋልና፡፡ ስለዚህም ነው ሰው በዚሁ ተፈጥሮ  እግዚአብሔርን ከመላእክት ይልቅ ይመስለዋል መባሉ፡፡
የነፍስ ተፈጥሮ ከተዋሐደችው ሥጋ ስለሚበልጥ እግዚአብሔር ለተዋሐደችው ሥጋ ሕይወት ሰጪ በማድረግ በሥጋና ለሥጋ በሆኑት ሁሉ ላይ ገዢና መሪ አድርጎ ሾማት፡፡ እርሷን ደግሞ የመናፍስት አምላክ ይገዛታል፡፡ አዳም የሥጋ ባሕርይውን በትክክል ማስተዋል የጀመረው እግዚአብሔር አምላክ ለምድር እንስሳት ሁሉ ስም ይሰጣቸው ዘንድ ወደ እርሱ ባቀረበለት ጊዜ ነበር፡፡
አዳም እንስሳት ጥንድ ጥንድ ሆነው ወደእርሱ ሲቀርቡ ተመለከተ፤ በዚህ ጊዜ ልቡ በከባድ ሃዘን ተመታ፣ አንዱ ጸሐፊ የአዳምን ብቸኝነት እንዲህ ይገልጸዋል “perfect solitude would turn a paradise in to a desert, and a palace in to dungeon” ፍጹም ብቸኝነት ገነትን ጭው ወዳለ በረሃነት፤ ቤተ መንግሥትን ወደ ወህኒ ቤት ሊቀይረው ይችላል፡፡" ግሩም ነው! እውነትም ነው! ምክንያቱም በሥጋው ተፈጥሮ የተቃራኒ ጾታ ፈቃድ ነበረውና፡፡ እግዚአብሔርም ይህንን ማድረጉ ያለ ምክንያት አልነበረም፤ አዳም ባሕርይውን እንዲገነዘብ እንጂ፡፡ አዳም በነፍስ ባሕርይው መላእክትን ቢመስልም ነገር ግን በሥጋው ባሕርይው ስለሚለይ፤ በሥጋው ባሕርይው እንስሳትን ቢመስልም በነፍስ ተፈጥሮ ስለሚለይ እንደ እርሱ የሆነ ፍጥረት ባለመኖሩ በዚያች የደስታ መፍሰሻ ገነት ውስጥ ቆዘመ ተከዘ፡፡ እናቱ ምድር ምስያውን ሳታስገኝለት ለዘላለም አሸልባለችና አዘነ፣ በብቸኝነት ተብሰከሰከ፡፡ ይህን ያስተዋለ እግዚአብሔርሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም የሚመቸው ረዳት እንፍጠርለትአለ፡
  እግዚአብሔር በአዳም ላይ ከባድ እንቅልፍ ጣለበት ነፍሱ ግን የእግዚአብሔር የአምላኳን ትንግርት የሆነ ሥራን ታስተውልና ትመለከት ዘንድ ዐይኖቿ ተገልጠዋል፡፡ እርሱዋም ከተዋሐደችው አካል እግዚአብሔር አንዲት አጥንትወስዶ ሴት አድርጎ ሲፈጥረት ታስተውል ነበር፡፡ ነፍስም የጌታዋን ከኀሊነት ተመልክታ እጹብ እጹብ አለች!! ሥጋ ከእንቅልፉ ሲነቃ ነፍስም ወደ ቀድሞ ስፍራዋ ስትመለስ አዳም በምድር ላይ በጾታ የማትመስለውን ነገር ግን በተፈጥሮ የምትስተካከለውን ሴትን ተመለከታት ወደዳትም ሚስቱም አደረጋት አዳም የእናቱን የምድርን ሞት ረሳ ፈጽሞም ተጽናና፡፡
ከማሁ ይኩን ለነ በከመ ፈቃደከ አሜን!!
እንደ ፈቃድህ ለእኛም ይሁንልን ይደረግልን አሜን!!

No comments:

Post a Comment