Saturday, August 11, 2012

ግሩም ድንቅ የሆነው ተፈጥሮ!!!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊ
06/12/2004
በመንፈሳዊው ዓለም ሴት ልጅ ላስተዋላት ከገነትም ይልቅ የምትረቅ ናት፡፡ እኔ ስለሴት ልጅ ሳስብ በአግርሞት እሞላለሁ፡፡ አንድ ወቅት እግዚአብሔርን እንዲህ ብዬ ጠየቅሁት፡- ስለምን ነፍስን ለብቻዋ አልፈጠርካትም ? ስለምን ሥጋን ማኅደሯ አድርገኽ ፈጠርካት ?አልኹት፡፡ ለካ የነፍስ መዳኗና አምላኩዋን የማየቱዋ ምክንያት ሥጋ ነበረች!!! ይህም የተፈጸመው በሴት ልጅ በኩል ነው፡፡ ከእርሱዋ ክርስቶስ ከአጥንቱዋ አጥንት ከሥጋዋም ሥጋ  ሆኖ በአካል ተገለጠ፡፡ ስለዚህም ለእርሱ ከአጥንቱ አጥንት ከሥጋው ሥጋ ስለሆነች ሴት ተባለች፡፡ ሴት ማለት ደግሞ ክፋዬ ማለት ነው፡፡ ክርስቶስ ከቅድስት ድንግል ማርያም የአዳምን ባሕርይ ነስቶ በመወለድ የእርሱዋ ክፋይ(ልጅ) ሲባል እኛ ደግሞ ከእርሱ ከክርስቶስ ከአጥንቱ አጥንት ከሥጋው ሥጋው በመሆን የእርሱ ክፋዮች(ልጆች) እንባል ዘንድ በጥምቀት ከሞቱ ጋር ተባበርን፡፡ 
ሴቶች በሔዋን ሴት ሲባሉ፡፡ እኛ ወንዶች ደግሞ በክርስቶስ በተመሰለውና የአቤል ምትክ በሆነው ሴት በኩል ሴት ተባልን፡፡ ይህ ደግሞ ድንቅ ነው!!! 
ታዲያ ስለምን ሴት ልጅ ከነስሙዋ ድንቅ የሆነች ፍጥረት አትባል? ጥበብን የሚወድ እግዚአብሔር ሴት ልጅን የፍጥረት ጉልላት አድርጎ ፈጠራት፡፡ ከእርሱዋም ስሙ ጥበብ የሆነ ክርስቶስ ተወለደ፡፡ በክርስቶስም እኛ ክርስቲያኖች በጥምቀት ከአጥንቱ አጥንት ከሥጋው ሥጋ በመሆን ተወለድን፡፡ 
አዲሱም አፈጣጠራችን ሔዋን ከአዳም የተገኘችበትን አፈጣጠር ይመስላል፡፡ አዳም አንቀላፍቶ ሳለ ሔዋን ከጎኑ አጥንት ተገኘች፡፡ እንዲሁ እኛም ክርስቶስ በሞት እንቅልፍ አንቀላፍቶ ሳለ ከጎኑ በፈሰሰው ደም ተዋጅተን ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ ነጽተን ዳግም ተፈጠርን (because we are members of His body of His flesh and His bones) እንዲል፡፡(1ቆሮ.12፡27) ታዲያ በመንፈሳዊ መረዳት ውስጥ ያለ ሰው እንዴት በሴት ልጅ ተፈጥሮ  አይደነቅ?

2 comments:

  1. “እናንተ የአሕዛብ ልጃገረዶች ሆይ ! ኑ ወደዚህ ቅረቡ ፣ አዲስ ምስጋናን ተማሩ ፤በእኅታችሁ በቅድስት ድንግል ማርያም በኩል ፣ ለምስጋና አንደበታችሁን ክፈቱ ፤ከእርሱዋ በመወለድ የመናገር ነጻነታችሁን ላጎናጸፋችሁ ምስጋናን አቅርቡ ፡፡” (ስብከት ወተግሣጽ) በጣም ድንቅ የሆነ ትምህርት ነው ወንድሜ

    ReplyDelete