Monday, January 14, 2013

ክርስትና ለእኔ እና እኔ አልስማማም እንዲሁም….



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
07/05/2005
ለእኔ ክርስትና ማለት ምን ማለት ነው ቢሉኝራስ መሆንብዬ እመልሳለሁ፡፡ በምን ሲባል ከኃጢአት በቀር በሁሉ ብዬ እመልሳለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ዕረፍት አለን፡፡ ክርስትና ድህነት ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን ስለፍቅርና ስለቅንነት እኛ ያለንን እንደ ችሎታችን የጠየቁንን ስለምንሰጥ ለሥጋዊው ድህነት የቀረብን ነን፡፡ ቢሆንም በሥራ ያን ጉድለት እንደፍነውና ለምጽዋት እጃችንን እንዘጋለን፡፡ ነገር ግን ለሁሉ ማለትም ለምድራዊውም ለሰማያዊውም ሀብታችን ምንጩዋ ቤተክርስቲያን ብትሆን መልካም ነበር፡፡ በእርሱዋ በኢኮኖሚም ሆነ በሥነ ልቡና የደከሙት ተጠነካክረው ለዓለም እንደ ብርሃን በመሆን በእነርሱ መልካም ሥራ የእግዚአብሔር ስም ሊመሰገን ይገባው ነበር፡፡

የዛን ጊዜ ክርስቶስን እንመስለዋለን ከመሰልነው ደግሞ ወደ ዕረፍቱ ገብተናል፡፡ አንድ ሆነን በአዲስ ተፈጥሮ በክርስቶስ ተፈጥረናልና አንድ እንሁን፣ እርስ በእርሳችን እንተሳሰብ እንተዛዘን እንጂ አንነካከስ፡፡ እንዴት ሰው የገዛ አካሉን በማድማትና በማቁሰል ዕረፍት ሊኖረው ይችላል? ስለዚህ አንድነታችን በፍቅር ማሰሪያ የታሰረ አንዱ የአካል ክፍል ከሌላው የአካል ክፍል ጋር ተሳስቦና ተመጋግቦ እንዲሁም ተረዳድቶ እንዲኖር እኛም እንዲሁ ብንኖር ያኔ በመንፈሱ የሚሰጠን ዕረፍት ታላቅ ይሆንልናለና ራስ እንጂ ጅራት አንሆንም በዚህም ራሳችንን ክርስቶስን እንመስለዋለን በዚህም ወደ ዕረፍቱ እንገባለን፡፡ ፍቅር በተግባር ናፍቃኛለች፡፡


እኔ አልስማማም ክርስትና ድህነት አይደለችም ፍቅር እንጂ 

ክርስቶስ እኛን ባለጠጎች ሊያደርገን ስለእኛ ደሃ ሆነ እንጂ ድህነት ክርስትና ናት አላለንም፡፡ እርሱ ወደ ቀደመ ክብራችን ሊመልሰንና አስቀድሞ ለእኛ ያሰበውን ሃሳብ ሊፈጽም መጣ፡፡ የእርሱም ዘለዓለማዊው ዕቅድ ሰውን በክርስቶስ በጸጋ አምላክ ሊያደረገው ነው፡፡ ስለዚህም ነው አስቀድሞም በእርሱ አርዓያና አምሳል መፍጠሩ፡፡ ቢሆንም ሰው ልክ እንደ እስራኤላዊያን 40 ቀን የምትፈጀዋን የሲናን በረሃ 40 ዓመት ሙሉ ተጉዞ ርስቱን ሊወርስ ስለፈቀደ ሞት የሚገዛውን ባሕርይ ገንዘቡ ሊያደርግ መረጠ፡፡ ምርጫውም እንደ እግዚአብሔር ሃሳብና ፈቃድ ስላልነበረ ኃጢአት በኃጢአትም ሞት ሰለጠነበት፡፡
ሰው ከመከራው ጽናት የተነሣ የእርሱን ሙሉ እርዳታን ባሻ ጊዜ እግዚአብሔር የእርሱ ፈቃድና አሳብ ምን እንደሆነ ሊያሳየንና በፈቃዳችን ብንታዘዘው እጅግ እንደሚያልቀንና እንደሚያከብረን ሊያስገነዝበን ልጁን እግዚአብሔር ወልድን ሂድ ውረድ ተወለድ ብሎ ላከው፡፡ እርሱም ተወልዶ የእርሱና የአባቱ ፈቃድ ምን እንደሆነ ገለጠልን፡፡ ያመነና በእርሱ ግንድነት ቅርንጫፍ ሆኖ ብዙ የጽድቅ ፍሬን ለማፍራት የወሰነና ሆኖ የተገኘ ዳነ፡፡ 
ሰው የመሆኑ አንደኛው ዓለማም ሰው ሁሉ በእርሱ ከመከራ ሥጋት እንዲያርፉ ነበር፡፡ ይህ ብቻ አይደለም እነርሱን አማልክት ሊያደርጋቸው ጭምር ነበር ፡፡ ሰዎች ሆይ ከእግዚአብሔር ጋር እየተማከረ የሚኖር መንፈስ ቅዱስ ልቡ የሆነለት ሰው እንዴት ጅራት ሊሆን ይችላል? የሰውን ሕሊና የፈጠረ እርሱ ልቡ የሆነለት ሰው እንዴት ከፍጥረታዊ ሰው በተሻለ ከፍታ ውስጥ ሊኖር አይቻለውም ተብሎ ይታሰባል? ስለዚህ ክርስቲያን ለዓለም ጥፋት ተጠያቂ ነው እላለሁ፡፡ ምክንያቱም እንደተፈጠረበት ዓላማ ራስ ሆኖ እየኖረ ስላልሆነ ነው፡፡ ራስ ሳይሆን ጅራት ሆኖአል ነፍሰ ገዳዮችና ገንዘብን የሚወዱ ሴሰኞችና ጨካኞች ጅራት መሆን ሲገባቸውራስሆነዋል፡፡ ስለዚህ እኔ አልስማማም ክርስትና ድህነት አይደለችም ፍቅር ናት እንጂ ፍቅር ደግሞ የሕግጋትና የእውቀት ሁሉ ቁንጮ ቁልፍ ናት የተያዘችውም በክርስቶስ አምኖ የመንፈሱ ቤተ መቅደስ በሆነ ክርስቲያን እጅ ነውና፡፡

ከዐሥርቱ ትእዛዛት የሚልቀው ሕግ

እኔ ከዐሥርቱ ትእዛዛትም የሚልቅ ሕግ በሐዲስ ኪዳን ተሰጥቶናል እላለሁ፡፡ ለምሳሌ ሕግና ነቢያት በእነርሱ የተንጠለጠሉትባቸው ሁለቱን ሕግጋት እንመለከት፡፡ በብሉይ ኪዳንእግዚአብሔር አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ኃይልህ በፍጹም ሰውነትህ በፍጹም ነፍስ ውደድየሚል ሕግ ተሰጥቶ ነበር፡፡ በሐዲስ ኪዳን ግን ከዚህ ሕግ እጅግ የሚልቅ ሕግ ተሰጥቶናል፡፡ ከክርስቶስ ጋር አንድ አካል ሁን ተዋሐድ የሚል ሕግ ማለት ነው፡፡ይህን ሕግ ስንፈጸም ክርስቶስ አካላችን ይሆናል እኛ ደግሞ እርስ በእርሳችን አንዱን አካል የምናገለግል ብሎቶች እንሆናለን፡፡ ለመሆኑ ለአንድ የሰውነት ክፍል አካልህን ውደድ ተብሎ ይነገረዋልን? ወይም ነገሩን ግልጥ ለማድረግ ዐይን ሆይ አካልህን ወደድ ይባላልን? አካሉ ነውና ትእዛዝን ሳይጠብቅ ይወደዋል፡፡
ለአንድ ክርስቲያንም እንደ ኦሪቱ እግዚአብሔርን ውደድ የሚለው ሕግ አይነገረውም ነገር ግን አንድ አካል ሁን ተብሎ ይታዘዛል፡፡ ክርስቶስ ግንድህ ሆኖ አንተ ቅርንጫፉ ሁን፡፡ እርሱ አካልህ ሆኖ አንተ የአካሉ ክፍል ሁን፡፡ እርሱ የወይራ ዛፍ ሆኖ አንተ ከወይራው ዛፍ የወይራ ዘይትን የምትሰጥ ቅርንጫፍ ሁን ተብሎ ትእዛዝ ይሰጠዋል፡፡ ወደ ሁለተኛው ሕግ እንምጣ፡፡ የብሉዩ ኪዳን ሕግባልንጀራህን እንደራስህ ውደድይላል፡፡
 ወደ አዲስ ኪዳን ሰትመጣ ግን ልክ አንድ የስንዴ ቅንጣት ወደ ዱቄትነት ተለውጦ ከሌሎች እርሱን ከመሰሉት ጋር አንድ ሕብስት እንዲሆን፤ ነገር ግን የስንዴው ቅንጣት የቅርጽ ለውጥ እንጂ የይዘት ለውጥ ሳይኖረው ከሌሎች የስንዴ ቅንጣቶች ጋር በውኃና እሳት አንድ ሕብስት እንዲሆን አንዲሁ ክርስቲያንም ከሌላው ክርስቲያን ወገኑ ጋር በውኃና እሳት በተባለው መንፈስ ቅዱስ ተጠምቆ አንድ አካል ይሆናል፡፡
በብሉይ ኪዳን ባልንጀራችንን እንደራሳችን እንድንወደው ነው የታዘዝነው፡፡ በሐዲስ ኪዳን ግን በአንድ አካል ውስጥ እርስ በእርሳችን አንድ በመሆን አንድ የሆነውን አካል እንድናገለግል ነው የታዘዘነው፡፡ ስለዚህ ከብሉዩ ይልቅ የሐዲስ ኪዳኑ ሕግ በእጅጉ ይልቃል፡፡ ይህን አስመልክቶ ቅዱስ ጳውሎስየምንባርከው የበረከት ጽዋ ከክርስቶስ ደም ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? የምንቆርሰውስ እንጀራ ከክርስቶስ ሥጋ ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? አንድ እንጀራ ስለሆነ እኛ ብዙዎች ስንሆን አንድ ሥጋ ነን” (1ቆሮ.1016-17)አለን፡፡
 ይህ በእውነት እግዚአብሔርን በፍጹም ሰውነትህ በፍጹም ኃይልህ በፍጹም ነፍስ በፍጹም ልብህ ውደድ ወይም ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ ከሚለው ሕግ በእጅጉ የሚልቅ ሕግ አይደለምን? የገዛ ሰውነትህን ውደድ ተብሎ የሚነገረው ሰው ማን ነው? የገዛ ሰውነቱንስ የሚጠላ ሰው ማን ነው? ክርስቶስ እርስ በእርሳችን የተጋጠምንበት አካላችን ነው፡፡ እርስ በእርሳችን ደግሞ ብልቶች ነን፡፡

No comments:

Post a Comment