Saturday, January 19, 2013

እኛ ታቦት ስንል መሠዊያ ማለታችን ነው


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
11/05/2005
በብሉይ ይፈጸም የነበረው ለሐዲስ ኪዳኑ ጥላ ነው፡፡ ስለዚህ ስለታቦት በተጻፈው ላይ እንደምናነበው በታቦቱ የላይኛው ክፍል ላይ ዙሪያውን አክሊል የሆነለት በግራና በቀኝ እንደሚናቸፉ አውራ ዶሮዎች ክንፎቻቸውን ወደ ላይ የዘረጉ በወርቅ የተሠሩ የኪሩቤል ምስሎች ያሉበት የስርየት መክደኛ ወይም mercy seat የሚባል ሥፍራ እንዳለ እንመለከታለን፡፡ በዚህ ላይ እግዚአብሔር ለሙሴና ለእስራኤላውያን በደመና አምድ ይገለጥላቸው ነበር፡፡(ዘፀ.2522338-11)
የስርየት መክደኛ ወይም mercy seat የሚለው ቃል ደግሞ እንደሚያመለክተን በላዩ ሥርየት የሚፈጸምበት እግዚአብሔር በምህረት የሚገለጥበት ስፍራ ነው፡፡ ነገር ግን ምንም እንኳ የሥርየት መክደኛ የተባለውን ስም ቢይዝም መሥዋዕት ሲቀርብበት አናይም፡፡ ይህም በእርሱ ላይ መቅረብ ያለበት መሥዋዕት ገና እንዳልመጣ የሚያሳየን ነው፡፡ ነገር ግን ሊቀ ካህናት ደሙን ይዞ በዚህ የስርየት መክደኛ አንጻር  ስለሕዝቡ ኃጢአት ማስተስረያ ከሚሆነው ደም ነክሮ በጣቱ ሰባት ጊዜ ይረጭ ነበር፡፡(ዘሌዋ.46) ይህም የሚያሳየን የደሙ ማረፊያ በዚያ ሥፍራ መሆን እንዳለበት ነገር ግን በዚያ ላይ ሊያርፍ የሚገባው ደም ገና እንዳልቀረበ ነው፡፡ በዚህም ይህ ደም ለጌታችን ቅዱስ ሥጋውና ቅዱስ ደም ምሳሌና ጥላ እንደሆነ መረዳት እንችላለን፡፡
በወርቅ የተሠሩት የኪሩቤል ምስሎችም የሚያመለክቱት አማናዊው መሥዋዕት በቀረበ ጊዜ አምላክ ነውና መላእክት ዙሪያውን ረበው ስለመገኘታቸው የሚያሳየን ነው፡፡ (ኢሳ.62-3) በእርግጥም በዚህ የስርየት መክደኛ ላይ እግዚአብሔር ይገለጥ እንደ ነበር እንዲሁ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሔር ነውና የቅዱስ ሥጋውና የክቡር ደሙ ማረፊያ መሆኑ ተገቢ ነው፡፡ የስርየት መክደኛው ወይም mercy seat የሚለው ስምም እንደ ስሙ አገልግሎት መስጠት የሚጀምረውም የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ሲያርፍበት ብቻ ነው፡፡
ይህ እንግዲህ ለሐዲስ ኪዳን እንደ ጥላ ነው፡፡ ስለዚህ ቤተክርስቲያን በምትታነጽበት ጊዜ ቅድስተ ቅዱሳን(ቅድስት) በምትባለው ስፍራ አማናዊውን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋ ክቡር ደም ለማቅረብ ታቦት ወይም የስርየት መክደኛ ወይም መሠዊያ ወይም mercy seat በመሥራት እንጠቀማለን፡፡ ስለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ መሠዊያ አለን ማለቱ፡፡(ዕብ.13፡15)እንዲህ ስለሆነ ግን ይህ መሠዊያ የብሉዩ ኮፒ መሆን አይጠበቅበትም፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር አምላክ በነቢዩ ሚልክያስከፀሐይ መውጫ ጀምሮ እስከ መግቢያዋ ድረስ ስሜ በአሕዛብ ዘንድ ታላቅ ይሆናልና በየስፍራውም ስለስሜ ዕጣንን ያጥናሉ ንጹሕም ቁርባን ያቀርባሉ”(ሚል.111) የሚለው የትንቢት ቃል በሐዲስ ኪዳን ተፈጽሞአልና ንጹሕ ቁርባን የሆነውን የጌታችንን የመድኀኒታችንን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም የምናሳርፍበት ሥፍራ ይህ መሠዊያ ነው፡፡ ይህን ቅዱስ ጳውሎስ የምህረት ዙፋን ይለዋል፡፡(ዕብ.416)

1 comment:

  1. ታቦት በኢትዮጵያ ውስጥ በልማድ ያለ አይደለም ወይም አንዳንድ የዋሆች እንደሚሉት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ ኦሪትን ከሥርዓተ ወንጌል ጋር ባባላንጣነት የምታታግል አይደለችም ፡፡ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ከክርስትና በፊት የብሉይ ኪዳን አገር የነበረችው ኢትዮጵያ በክርስትና ጊዜም ከብሉይ ኪዳን ያገኘቻቸውን ጠቃሚ ነገሮች በክርስትና መንፈስ እየተረጎመች ትጠቀምባቸዋለች ፡፡ ከብሉይ ኪዳን ከወሰደቻቸውም አንዱ ጽላተ ኪዳን ታቦተ ሕግ ነው ፡፡ አዲስ ቤተ ክርስቲያን በሚሰራበት ጊዜ ከእጽ ወይም ከእብነ በረድ ተቀርጾ በላይ የእግዚአብሔር ምስጢራዊ ስም (ህቡእ ስም) ((አልፋ ኦሜጋ)) የመጀመሪያውና የመጨረሻው ማለት ነው ፡፡ ይህ ቃል ከተጻፈበት በኋላ በኤፒስ ቆጶሱ እጅ ተባርኮና ሜሮን ተቀብቶ በመንበሩ ይሰየማል (ይቀመጣል) ፡፡ በቅዳሴም ጊዜ ሕብስቱና ወይኑ ወደ ቤተ መቅደስ ሲገባ ቄሱ ሥርዓተ ቅዳሴውን የሚያከናውነው ሕብስቱን ሥጋ መለኮት ፣ ወይኑን ደመ መለኮት ወደ መሆን የሚለውጠው በዚህ በታቦቱ ላይ ነው ፡፡ የደብተራ ኦሪት ጽላት እግዚብሔር በደመና ተከናንቦ ሙሴንና አሮንን የሚያነጋግርበት ለእስራኤል ብቻ በረድኤት የሚገጥበት ዙፋን ነበር ፡፡ ይህ ግን የአምላክ ሥጋና ደም የሚፈተትበት ሥጋዬን የበላ ደሜን የጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው ፡፡ ሥጋዬን ብሎ ደሜንም ጠጡ እያለ ያመኑትን ሁሉ የሚጠራበት የምሕረት ምሥዋዕ (መሠዊ) ነው ፡፡ ክብርና ስግደትም የሚደረግለት ስለዚህ ነው ፡፡


    አባ ጎርጎርዮስ ፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ገጽ 95
    “ከኢትዮጵያም ሌላ በምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ታቦት የተለመደ ሕግ ነው ፡፡ ሥጋውን ደሙን የሚፈትቱት በታቦቱ ላይ ነው ፡፡ ለምሳሌ ግብጻውያን ታቦቱን ሉህ ይሉታል ፡፡ ጽላት ሰሌዳ ማለት ነው ፡፡ ያለ እርሱ ሥጋውንና ደሙን አይፈትቱም ፡፡ የምሥራቅ አብያት ክርስቲያናት ተብለው የሚጠሩት የግሪክ የሩሲያ የሩሜንያና ሌሎችም ወደ ክርስትና የተመለሱት ከአረማዊነት ስለሆነ የታቦትን ምሥጢር አያውቁትም ፡፡ በታቦቱ ፈንታ ከመንበር የማይነሳ እንደ ታቦት የሚከበር የጌታ የስቅለቱ ወይም የግንዘቱ ስዕል ያለበት የነጭ ሐር መጎናጸፊያ አላቸው ፡፡ ያለ እርሱ ሥጋውን ደሙን አይፈትቱም ፡፡ ይህንን በጽርእ ((አንዲሚንሲዮን ይሉታል ፡፡ ((ህየንተ ታቦት)) ስለ ታቦት ፈንታ ማለት ነው ፡፡ የሮማ ካቶሊኮች ሜንሳ ይሉታል ጠረጴዛ ማለት ነው ፡፡ ))

    ቤተ ክርስቲያናችን በሙሴና በክርስቶስ ፣ በብሉይና በሐዲስ ወይም በጣዖትና በእውነት በምሳሌና በአማናዊ ያለውን ልዩነት ስለምታውቅ ለሚጠይቂዋት ሁሉ ይህን እምነቱዋን ከማስረዳት ተቆጥባ አታውቅም ፡፡ ታቦት በሐዲስ ኪዳንም በቤተ ክርስቲያናችን አምልኮተ እግዚአብሔር ይፈጸምበታል ፡፡ ታቦት እውነተኛው የሕይወት ምግብ የክርስቶስ ሥጋና ደም የሚቀርብበትና የሚፈተትበት መሠዊያ ነው ፡፡ የሚከበረውና የሚሰገድለትም ስለዚህ ነው ፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የምትጠቀምበት ታቦተ ምሥዋዕ (መሠዊያ) ቅዱስ ቁርባን የሚከብርበት ነው እንጅ እንደ ብሉይ ኪዳን የምንጠቀምበት አይደለም

    የኘሮቴስታንት ታቦት
    1. ጠረጴዛ ነጭ ልብስ አልብሰው ሕብስትና ወይን በዚያ ላይ ያስቀምጣሉ በፊቱ ይንበረከኩና ይሰግዳሉ ፡፡ በጠረጴዛው ግራና ቀኝ አልፎ አልፎ ሻማ ወይም አበባ ያስቀምጣሉ ፡፡ በአባ እስጢፋኖስ ተመክረው ይሆን ይህን የሚያደርጉት
    2. ባዶ ወንበር - ጌታ ወደ ጉባኤያችን መጥቶ ይቀመጥበታል ብለው ሲለሚያምኑ ባዶውን ከፓስተሩ ጎን የሚቀመጥ ነው ፡፡ ወይም ከፊት ለፊት ካሉት ባዶ ወንበሮች አንዱን ክፍት ያደርጋሉ
    3. በጠረጴዛ ላይ የተቀመጠ የተከፈተ መጽሐፍ ቅዱስ ፣ ሲያስፈልግም ከፍ አድርገው በማንሳት ክብር ይሰጣሉ
    4. የተለያዩ ቁሳቁሶች - እኒህ ደግሞ መንፈስን ለመጎተት ወይንም ከመንፈስ ለመገናኘት የሚጠቀሙበት ነው ፡፡ ፖይንት ኦፍ ኮንታክት በመባል ይታወቃል http://www.ethiopianorthodox.org/amharic/holybooks/seweruadega.pdf

    ReplyDelete