Friday, January 11, 2013

ፍትሐት በቤተክርስቲያን እንዴት?




በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/05/2005
“ስለሙታን የሚጠመቁ ምን ያደርጋሉ ሙታንስ ከቶ የማይነሡ ከሆነ ስለእነርሱ የሚጠመቁ ስለምንድር ነው”(1ቆሮ.15፡29)
ጥምቀት ሰውን ከኃጢአት አንጽቶ የእግዚአብሔር ልጅነት ሥልጣንን በመስጠት ዳግም የሚወለዱበት ጌታችን የመሠረተልን ሥርዐት ነው፡፡ ነገር ግን ጥምቀት ስንል በመጽሐፍ ቅዱስ አንድ ዓይነት ትርጉም ብቻ የሚሰጠው አይደለም፡፡ ስለሌሎችም መከራን መቀበል በራሱ ጥምቀት ነው፡፡ ጌታችን ስለእኛ የተቀበለውን ሞት ጥምቀት ብሎት እናገኘዋለን፡፡ “እኔ ልጠጣው ያለውን ጽዋ ልትጠጡ እኔም የምጠመቀውን ጥምቀት ልትጠመቁ ትችላለችሁን፡፡”(ማቴ.20፡22)

 በሌላ ቦታ ደግሞ ቅዱስ ጳውሎስ “እግዚአብሔር ሙላቱ ሁሉ በእርሱ እንዲኖር በመስቀሉ ደም ሰላምን አድርጎ በምድር ወይም በሰማያት ያሉትን ለራሱ ሊያስታርቅ ፈቅዶአልና” ተብሎ ተጽፎልን እናገኛለን፡፡(ቆላ.1፡19) ይህ ቃል በጥልቀት ስንመለከተው በሰማያት የክርስቶስ የደሙ ቤዛነት የሚያስፈልጋቸው እነማናቸው? የሚልን ጥያቄን ይፈጥርብናል፡፡፡ ቃሉንም ስንመለከት “ፈቅዶአልና” የሚለው ቃል ቀጣይነት ያለው ግሥ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ እናም እነማናቸው በሰማያት የመስቀሉ ቤዛነት የሚያስፈልጋቸው ብለን ስንጠይቅ በሰማያዊ ሥፍራ ያሉ አጋንንት ወይም ቅዱሳን መላእክት ሳይሆኑ በሲኦል ያሉ ነፍሳት እንደሆኑ ግልጥ ይሆንልናል፡፡
በሲኦል የነበሩ ነፍሳት እንደ እኛ በውኃና በመንፈስ ተጠምቀው ሳይሆን የዳኑት በእርሱ አምነው የነበሩትነ በመስቀል ላይ አንድ ጊዜ ግን ለዘለዓለም ባቀረበው መሥዋዕት እንደሆነ ለሁላችን ግልጥ ነው፡፡ (ዕብ.11 በሙሉ) ይህም እነርሱን በመስቀሉ በተፈጸመው የቤዛነት ሥራ ከሲኦል እንዲወጡና ወደ ገነት እንደፈለሱ ረድቶአቸዋል፡፡ “ፈቅዶአልና" የሚለውን ግሥ እንሚያስረዳን ደግሞ አሁንም ይህ አገልግሎት እስከ እለተ ምጽአት ድረስ እንደሚቀጥል ነው፡፡  ስለዚህም ለእነርሱ መሥዋዕቱ ጥምቀት ሆኖአቸዋል ማለት ነው፡፡ 
እኛም ብንሆን በውኃና በመንፈስ ተጠምቀን ከክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ጋር የምንተባበር ሆነናል፡፡ ያም ማለት ጥምቀታችን ከመሥዋዕቱ ጋር ኅብረት እንደዳለወው እንረዳለን፡፡(ሮሜ.6፡3-4) ስለዚህ በእርሱ አምነው የሞቱ ነገር ግን የሥነምግባር ሕጸጽ  ያለባቸው ክርስቲያኖች በቤተክርስቲያን በኩል የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አማናዊው መሥዋዕት ይቀርብላቸዋል፡፡ እርሱም እነርሱን ንጹሐን በማድረግ ወደ መንግሥቱ እንዲፈልሱ ያበቃቸዋል፡፡
እንዲህም ስለሆነ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “እርሱ ግን ለዘለዓለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው ስለ እነርሱ ሊያማልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህም ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል”አለን፡፡(ዕብ.7፡24-25) 
ይህን እንዴት እንረዳዋለን? ቅዱስ ዮሐንስ “በዙፋኑና በአራቱ እንስሶች መካከልም በሽማግሌዎችም መካከል እንደ ታረደ በግ ቆሞ አየሁ”(ራእይ.5፡8)ብሎ ጽፎልናል፡፡ “ቆሞ አየሁ” የሚለው ኃይለ ቃል ለዘለዓለም መሥዋዕት አድርጎ ራሱን ማቅረቡን ያሳየናል፡፡ ስለዚህም ይህ ኃይለ ቃል ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ሲያስታርቅ ይኖራል የሚለውን ትርጉም ይሰጠናል፡፡(ዕብ.10፡19-20)በዚህም መሠረት “ቆሞ አየሁ” የሚለው ቃል “እርሱ ግን ለዘለዓለም የሚኖር ስለሆነ የማይለወጥ ክህነት አለው ስለ እነርሱ ሊያማልድ በሕይወት ይኖራልና” የሚለውን ይተረጉምልናል፡፡ ጌታችን ስለእኛ ኃጢአት ስርየት"ታርዶአል ግን ቆሞአል" በዚህም ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ለዘለዓለም ማቅረቡን እንረዳለን፡፡ "ሲያማልድ" ሲለንም ሲያስታርቅ እንደሆነ ግልጥ ነው፡፡ እንዲህም ሲል ከራሱ ጋር ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ማለቱ ነው፡፡
ስለዚህም “ስለእነርሱ ሊያማለድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና” ሲል “እንደ ታረደ በግ ቆሞ አየሁ” እንዲል ራሱ መሥዋዕት፤ ራሱ መሥዋዕት አቅራቢ ሆኖ “በዙፋኑና በአራቱ እንስሶች መካከልም በሽማግሌዎችም መካከል” የሚለው ቃል እንደሚያስረዳን በዚያ ቦታ ሊኖር የሚገባው እግዚአብሔር ብቻ ስለሆነ(ራእይ.4፡8-10) ራሱ መሥዋዕት ተቀባይ መሆኑን እንረዳለን፡፡ በዚህም መሥዋዕት በእርሱ አምነው የሞቱ ነገር ግን የምግባር ሕጸጽ ያለባቸው አንድ ጊዜ ለዘለዓለም በቀረበው መሥዋዕት ነጽተው ወደ ገነት እንደሚገቡ እንረዳለን፡፡ ስለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ “እግዚአብሔር በመስቀሉ ደም ሰላምን አድርጎ በሰማያት ወይም በምድር ያሉትን ለራሱ ሊያስታርቅ ፈቀዶአልና” ማለቱ፡፡ ስለዚህ “የልጁም የኢየሱስ ክርቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻል”(1ዮሐ.1፡7) ይላልና በምድር ያለነው ሕያዋን ለሙታን ወገኖቻችን ተገብተን ከኃጢአታቸው ነጽተው ወደ ገነት እንዲፈልሱ ይህን በሰማያትም በምድርም ያሉት ነፍሳት ከራሱ ጋር የሚያስታርቀውን አማናዊ መሥዋዕት በቤተክርስቲያን የምናቀርበው፡፡ ይህም ለሙታን እንደ ጥምቀት ይሆናቸዋል ማለትም አድሶ ወደ ገነት እንዲፈልሱ ያደርጋቸዋል፡፡  

1 comment:

  1. ይህ ነገር በጣም ከባድ ትምህርት ይመስለኛል::
    ""በእርሱ አምነው የሞቱ ነገር ግን የሥነምግባር ሕጸጽ ያለባቸው ክርስቲያኖች በቤተክርስቲያን በኩል የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አማናዊው መሥዋዕት ይቀርብላቸዋል፡፡ እርሱም እነርሱን ንጹሐን በማድረግ ወደ መንግሥቱ እንዲፈልሱ ያበቃቸዋል፡""
    ከ Universalist ትምህርት የሚለየው ምንድነው? ሁለተኛ እድል የሚባል ነገር ካለ የሚመሳሰሉበት ነጥብ ይሆናል::".....ሰማያት ያሉትን ለራሱ ሊያስታርቅ ፈቅዶአልና” የሚለው በክርስቶስ ቤዛነት ከሲ ኦል የወጡትን ነፍሳት ላለመሆኑ እና እስካሁንም ቀጣይ መሆኑን እንዴት እርገጠኛ እንሆናለን? እመሰግናለሁ::

    ReplyDelete