Monday, March 16, 2015

አራቱ ልደታት

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 

06/07/2007

የክርስቲያን አፈጣጠሩና እድገቱ እጅግ ግሩም ነው። ልደቱ ፍጥረታዊና መንፈሳዊ ብለን ለሁለት ከፍለናቸው ልንመለከታቸው ብንችልም ሁለትም ሦስትም  መንፈሳዊ ልደታት አሉት። ሁሉም ግን መሠረታዊያን ናቸው።
ሰው ከእናትና ከአባቱ አስቀድሞ ሳይፈጠር መንፈሳዊው ልደት ሊፈጸምለት አይችልም። ስለዚህ ፍቅር በሆነው አምላክ በሥጋ ሰው ሆኖ ሊፈጠር ይገባዋል። ይህ ልደት ግን በቂ ነው አይባልም። ሌላ አባ አባ የሚልበትን ልደት ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ በስመ ሥላሴ ሊወለድ ይገባዋል።
ይህም በራሱ ሙሉ አያደርገውምና አዲስ ለተፈጠረበት ተፈጥሮ ክርስቶስን ወደመምሰል ማደግ ይጠበቅበታል። ይህ ክርስቶስን የመምሰል ደረጃ ሦስተኛ ልደት ይባላል። ይህም ክርስቶስን በተግባር ወደ  መምሰል የመምጣት ሂደት ነው። ወደዚህ መንፈሳዊ ከፍታ  የደረሰ ሰው ላይ ክርስቶስ በእርሱ ይገለጣል።  ሰዎች ሁሉ የክርስቶስን መልክ በእርሱ ላይ ይመለከታሉ። ነገር ግን ደግሞ ሌላ አራተኛ ልደት ያስፈልገዋል። እርሱም በትንሣኤ ለድል አድራጊዎቹ ከክርስቶስ የሚሰጥ ልዩና ዘለዓለማዊ ስጦታ ነው። ክርስቶስ በትንሣኤ ሥጋችንን እንደ ራሱ ሥጋ አድርጎ በመለወጥ ልክ በደብረ ታቦር ወደ አሳየን ክብሩ በማሸጋገር የምንወለድበት ልደት ነው። ይህን ዓይነት ልደትን በምሳሌነት አስቀድሞ በሙሴ አሳይቶን ነበር። እውነተኛውን ልደት ግን በትንሣኤ የእርሱን ሥጋ እንዲመስል አድርጎ ሥጋችንን በመለወጥ ይሰጠናል። ይህን አስመልክቶ ጌታችን በቃሉ "እውነት እላችኋለሁ፥ እናንተስ የተከተላችሁኝ፥ በዳግመኛ ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በሚቀመጥበት ጊዜ፥ እናንተ ደግሞ በአሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገድ ስትፈርዱ በአሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ።"(ማቴ.19:28) ብሎናል። በእውነት እርሱ ለዚህ ክብር የፈጠረን ጌታ ፍቅር የሆነውን ሰውነቱን ለብሰን ለዘለዓለም ስናመሰግነው እንድኖር ያብቃን። ለዘለዓለም አሜን።

No comments:

Post a Comment