Thursday, June 8, 2017

የነፍስ ወግ ሦስተኛ ክፍል በእንተ ትዳር

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
02/10/2009
ትዳር መልካም ነው፡፡ የትዳርን ትርጉም ከዚህ በፊት እንደጻፍኹላችሁ በገዛ ሰውነታችን ውስጥ በምሳሌነት እናገኘዋለን፡፡  ይህ ደግሞ የሚደንቅ ነው፡፡ ይህንንም በልጆቻችን እንመለከተዋለን፡፡ እነርሱ የአንድነታችን ውጤቶች ናቸው፡፡ ቢሆንም ከዚህ በፊት በዚህ ጉዳይ ላይ ሰፊ ትንታኔ የሰጠሁ ስለመሰለኝ ለዛሬ በዚህ ላይ ብዙ አልልም፡፡ ልብ እንድትሉ የምፈልገው ነገር ግን በነፍስና በሥጋ መካከል ያለው ተዋሕዶ የትዳር አምሳያ መሆኑን ነው፡፡ እረ እንደውም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቃል ከሥጋና ነፍስ ጋር በማኅፀን በተዋሕዶ አንድ መሆኑ የትዳር አምሳል እንደሆነ ያስተምረናል፡፡ እናም ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው ገና በጽንሰት ጊዜ መለኮትና ሥጋ አንድ በሆኑበት ቅጽበት ነበር፡፡ ስለዚህም በዚህ የሥጋው መጋረጃ በኩል ወደ ቅድስት መግባትን አግኝተናል:: እርሱም ከእናቱ ከቅድሰት ድንግል ማርያም የነሣው ሥጋ ነው፡፡ ይህ ሰውነቱ የገነት አምሳያ ስለሆነ ቅዱስ ኤፍሬም በተወጋው ጎኑ በኩል ወደ ገነት መግባትን አገኘን ብሎ ያስተምራል፡፡ በእርግጥም ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ ነጽተን ከጎኑ በፈሰሰው ደም ተዋጅተን በእኛ ችሎታ ሳይሆን በእርሱ ቸርነት የክርስቶስ የአካል ሕዋሳት ለመሆን በቅተናል፡፡ ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን በሆነችው ሰውነቱ በኩል መዳናችን ተፈጸመ፡፡ ሁሉ የእርሱ ከእርሱ ለእርሱ በእርሱ የሆነው ይህ ምስጢር እንዴት ድንቅ ነው!!

ከጎኑ ከተገኘች ውኃ ተጠምቀን ከኃጢአታችን ነጻን፤ የውድቀት ባሕርያችንም ተወግዶ በትንሣኤ እርሱን ለብሰን እንድንነሣ አርቦነ መንፈስ ቅዱሰን በሰውነታችን ላይ አተመው፡፡  "የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነው" እንዲል ስለመተላለፋችን ደሙን በማፍሰስ የደሙ ሙሽሮች አደረገን፡፡  ኃጢአታችንን ለካህን ብንናዘዝ በካህኑ አድሮ ይቅር የሚለን እርሱ ነው፡፡ የእርሱ በሆነው ቅዱስ  ሥጋውና ክቡር ደሙ እርሱ በእኛ እኛም በእርሱ እንድንኖርና በሰማያዊ ሥፍራ ከአእላፍት መላእክት፣ ከበኩራት ማኅበር ፣ ከቅዱሳን ነፍሳት ጋር አንድ ቤተ ሰብ እንድንሆን አበቃን፡፡ በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ በምድር ሆነን በሰማያት በሰማያዊ ሥፍራ እንድንገኝ አደረገን፡፡ ይህ ሁሉ የሚፈጸመው ከቅድሰት ድንግል ማርያም በተካፈለው ሥጋና ደም ነው፡፡
ይህ ግሩም የሆነ ምሥጢር እነሆ በምድር ባለችው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ይፈጸማል፡፡ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በማየ ገቦዉ ተጠምቀን ቅዱስ ሥጋውን በልተን ክቡር ደሙን ጠጥተን የእግዚአብሔር ልጅነት ስልጣንን በመቀበል የቅዱሳን ጉባኤ ወደተባለችው ሰማያዊቱ ቤተ ክርስቲያን እንገባለን፡፡
ይህች በዓይን ስትታይ በቦታ የተወሰነች ጠባብ ሥፍራ ስትሆን በመንፈሳዊው ዓይን ስትታይ ግን አእላፍ መላእክት የከተሙባት፣ ከምድር እስከ ሰማይ በአምደ ብርሃን መልክ የተተከለች ቅዱሳን ነፍሳት የሚኖሩባት ክርስቶስም በእምነት ወደ እርሱ ለሚቀርቡት ሁሉ አንዴ ግን ለዘለዓለም ባቀረበው መሥዋዕት በምሕረት የሚገለጥባት ለቦታዋ ወሰን ለጊዜ ልኬት የሌላት መላእክት የሚወጡባት የሚወርዱባት ሥፍራ ናት፡፡
የቃል ሥጋ መሆን ቤተ ክርስቲያን በአካል እንድትገለጥ አድርጔታል፡፡ እርሷም የክርስቶስ ሰውነት ናት፡፡
በእርሱ “አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም ባሪያም ጨዋ ሰውም የለም ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና”(ገላ.3፡28)እንዲል አንድ ሰው ሆነናል፡፡ በብሉይ የነበሩ እርሱን ተስፋ አድርገው የኖሩ፣ በክርስቶስ አምነው ክርስቶስን በሁሉ መስለው የኖሩ ሐዋርያትና  ከእነርሱ በኋላ የተነሡ ክርስቲያኖችና አሁን በሥጋ ሕያዋን የሆንን እኛ በዚህ አንድ ሰውነት ተጠቅልለናል፡፡ በዚህ ሰውነት አንድ ጉባኤ፣ አንድ ቤተሰብ፣ አንድ አካል፣ አንድ መንጋ ሆንን፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ “እናንተም የክርስቶስ አካል ናችሁ እያንዳንዳችሁም ብልቶች ናችሁ፡፡”(1ቆሮ.12፡27) ብሎ አተማረን፡፡ እርሱ እግዚአብሔር ቃል በማኅፀን ከሥጋ ጋር ጋብቻን በመፈጸሙ ምክንያት በእርሱ መልካምን ለመሥራት ዳግም ተፈጠረን፡፡ ውኃው ከጎኑ የተገኘ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስም የባሕርይ ሕይወቱ ነው፡፡ በእነዚህ በሁለቱ ዳግም እኛን በመፍጠር ልጆቹ አደረገን፡፡
እናም ወዳጆቼ ይህችን የትዳር ትርጉም ተምሳሌት የሆነችውን ተፈጥሮ አንዴ በእኛ ሌላ ጊዜ በቃልና በሥጋ ሌላ ጊዜ ደግሞ በክርስቶስና በቤተ ክርስቲያን መስለን ተመለከትናት፡፡
 በዚህ ጽንሰ ሃሳብ ላይ በጥልቀት የጻፈልንም ደግሞ ቅዱስ ጳውሎስ ነው፡፡ እስቲ ከቅዱስ ጳውሎስ አስተምህሮ ተነሥተን ስለ ትዳር እንነጋገር ቅዱሱ:-
"የወንድ ሁሉ ራስ ክርስቶስ፣ የሴት ራስ ወንድ፣ የክርስቶስ ራስ እግዚአብሔር እንደሆነ ልታውቁ እወዳለሁ” አለን፡፡  እንዲሁም “ክርስቶስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ራስ እንደሆነ ባል የሚስት ራስ ነው” ብሎም አስተማረን፡፡ ይህ ሐዋርያ በዚህ መልእክቱ ክርስቶስን፣ ወንድን፣ እግዚአብሔርን ራስ ብሎ እንደጠራቸው እናስተውላለን፡፡  እነዚህ ሁሉ ራስነቶች ግን ለአንዱ ለእርሱ ለክርስቶስ የተነገሩ ናቸው፡፡ የወንድ ራስ ክርስቶስ ለሚለው፡- እርሱ ክርስቶስ ለቤተ ክርስቲያን ራስ ሆነው ለተሾሙ የሐዋርያትን ስልጣን ለያዙ ካህናት ራስ ነው(ለክህነት የሚሾሙት ወንዶች መሆናቸውን ልብ በሉ) ሲለን ነው፡፡ ወንድ የሴት ራስ ነው ሲልም፡- ነቢዩ “ወንድ ልጅ ተሰጠን” እንዲል  እርሱ ክርስቶስ በሴት ለተመሰለችው ቤተ ክርሰቲያን ራሷ ነው(በዚህ ካህናቱም ይካተታሉ)ሲለን ነው፡፡ “የክርስቶስ ራስ እግዚአብሔር” ሲልም በእርሱ አንድ ሰው ለተባልነው ለእኛ እንደ እግዚአብሔርነቱ ራስ መሆኑን ሲያስረዳን ነው፡፡ በክርስቶስ ሰውነት ነውና አንድ አካል የሆነው፡፡ አካላችን የክርስቶስ አካል ነው፡፡ ይሀንን ቅዱስ ጳውሎስ “ሥጋችሁ የክርስቶስ ብልቶች እንደ ሆነ አታውቁምን? እንግዲህ የክርስቶስን ብልቶች ወስጄ የጋለሞታ ብልቶች ላድርጋቸውን? አይገባም”ብሎ አስረዳል፡፡ (1ቆሮ.6፡15)ስለዚህ እንደ እግዚአብሔር እርሱ ለእኛ ራሳችን ነው፡፡ በእርሱ ላይ አብ ራስ አይደለም፡፡ በራስነት አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ አንድ ናቸው፡፡ በእርሱ አካል ውስጥ ተጠቃለን በእርሱ አንድ ሰው ለተባልን ለእኛ አብም ወልድም መንፈስ ቅዱስም ራሳችን ነው፡፡  ሰለዚህ ሐዋርያው ሦስቴ ራስ፣ ራስ ፣ ራስ ያለው እርሱን ክርስቶስን መሆኑን በዚህ መረዳት እንችላለን፡፡ በሌላ ስፍራ ደግሞ "በደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን" በማለት በደሙ የዋጃትን ክርስቶስን እግዚአብሔር ሲለው እናገኘዋለን፡፡
ይህን ወደ ትዳር ሕይወት ስናመጣው ክብር ምስጋና ይግባውና ለባል ራሱ ክርስቶስ ነው፡፡ እርሱ ለክርስቶስ ሊገዛ ቤቱንም እንደ ክርስቶስ ሃሳብና ፈቃድ ሊመራ ይገባዋል፡፡ እንዲህ ዓይነት ሰው እግዚአብሔርን መፍራት በውስጡ ስላለ ክርስቶስንንና ትምህርቱን ዘወትር ስለሚያስብና ዘወትር ራሱን ከኃጢአት ለመጠበቅ ስለሚተጋ እርሱ ለቤተሰቡ እንደ ብርሃን ሆኖ በቀና መንገድ ሊመራ ብቃቱን ይኖረዋል፡፡ ይህ አገዛዝ ከስህተት በፊት በአዳምና በሔዋን መካከል ያለውን አገዛዝን ይመሰላል፡፡ ምክንያቱም ሚስቱና ልጆቹ ከርሱ የሰሙትን ከእግዚአብሔር አንደሰሙ ቆጥረው ለቃሉ ይታዘዙለታልና፡፡ በእነርሱ ዘንድ ማዘዝና መታዘዝ ቀንበር አይደለም፡፡ ቢታዘዙ የታዘዙት ሊታዘዙት ለሚገባ ለእግዚአብሔር ነውና፡፡
 ስለዚህ ለባል ከውድቀት በፊት ያለውን ሕይወት በትዳር ውስጥ ሊያይ ከወደደ ክርስቶስን ማወቅ ማወቅ ብቻ ሳይሆን የሕይወቱ መርሕ አድርጎ ሊመላለስ ይገባዋል፡፡ ይህ የወንድ ልጅ ሸክሙ ነው፡፡ እንደ ነፍሱ ክርስቶስን አድርጎ በእርሱ እስትንፋስነት የማይመላለስ ወንድ የትዳር ሕይወቱ ጣዕም የለውም፡፡ ስለዚህም ነው ሐዋርያቱ “የባልና የሚስት ሥርዓት እንዲህ ከሆነ መጋባት አይጠቅምም” (ማቴ.19፡10) ማለታቸው፡፡ ምክንያቱም ትዳር ማለት ነፍስንና ሥጋ ሆኖ መኖር ማለት ነውና፡፡ ከዚህ ውጪ ከሆነ ትዳር ወይኒ ቤት ይሆናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም “እኔ ግን ለተጋቡት አዝናለሁ” ብሎአል፡፡ ምክንያቱም እንደ ሥነ ተፈጥሮአቸው ነፍስና ሥጋ ሆነው መኖር ስለተሳናቸው ነው፡፡ ሆነው ሲገኙ ግን አዳምና ሔዋን  ከውደቀት በፊት ያላቸውን ሕይወት በመሰለ አኗኗር ውስጥ ይኖራሉ፡፡
የቤታቸውም ራስ እርሱ እግዚዚብሔር ይሆናል፡፡ ቤቱም ክርስቶስ እንደሚመራው እንደ አቂላና ጵርስቅላ ቤት ይሆንላቸዋል፡፡ ለእነዚህ ጥንዶች  “ነገር ግን እንዲህ በሚያደርጉ በሥጋቸው ላይ መከራ ይሆንባቸዋል፥ እኔም እራራላችሁ ነበር” የሚለው የቅዱስ ጳውሎስ ቃል አይሠራም፡፡ እኝህ ጥንዶች ለቅዱስ ጳውሎስ ቀኝ እጅ ነበሩ፤ በቅናት ሆኖ ስለክርስቶስ ይሰብክ የነበረውን አጵሎስን ክርስትና ጠላትነትን በሚፈጥሩ በስሜትና በቅናት የምትሰበክ አይደለችምና አስተምረውና አርቀው በማስተዋልና በፍቅር እንዲሰብካት ቤተ ክርስቲያን ወደ ሆነችው ቤታቸው ወስደው የመከሩትና ያስተማሩት ናቸው፡፡ ከዚያ በኋላ የቅዱስ ጳውሎስ ቀኝ እጅ በመሆን “እኔ እተክላለሁ አጵሎስ ያጠጣል” ተብሎ ተጻፈለት፡፡
 ለእነዚህ ጥንዶች “ያገባው ግን ሚስቱን እንዴት ደስ እንዲያሰኛት የዓለምን ነገር ያስባል፥ ልቡም ተከፍሎአል … የተጋባች ግን ባልዋን እንዴት ደስ እንድታሰኘው የዓለምን ነገር ታስባለች”(1ቆሮ.7፡33-34) የሚለው ትምህርት አይሠራም፡፡ ምክንያቱም ሁለቱም ስለ ራሳቸው ደስታ ሳይሆን ስለክርስቶስ ደስታ የሚተጉ ናቸውና፡፡ አንዱ ከአንዱ የሚሻው ክርስቶስን ነው፡፡ ለዚህ መረዳት አንክሮ ይገባል፡፡ ይህ ግን የሚሆነው ወንድ ራሱ የሆነውን ክርስቶስን ሲያውቀው ሲወደውና ሲመስለው ነው፡፡
ቢሆንም ግን ይህ የክርስቶስ ዘለዓለማዊ ሃሳቡ ነው እንጂ ነገሮች ሲከሰቱ ለመፍትሔ የመጣ ሃሳብ እንዳልሆነ ማንም ሊረዳው ይገባል፡፡ የክርስቶስ ራሰነት የባሕርይው እንደሆነ እንዲሁ የወንድ ልጅ ራስነት ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ሴት ልጅ አካል ስለመሆኗ አዳም “ይህች አጥንት ከአጥንቴ ሥጋዋም ከሥጋዬ ናት ስለዚህ ሴት ትባል” ብሎ ገልጦታል፡፡ “ከአጥንቴ አጥንት ከሥጋዬ ሥጋ” ሲላት “አካሌ ናት” ሲል እንደሆነ ማንም ልብ ይለዋል፡፡ በእውነትም ከአካሉ የተገኘች አካሉ ናትና፡፡
 እግዚአብሔር አምላክ የወንድ ልጅ ራስነት ሚና በሥራ እንዲገለጥም አስቀድሞ አዳምን ፈጥሮ ሕግን ሰጠው፤ ከጎኑ አጥንት ለተፈጠረችውም ሴት መምህር አደረገው፡፡ በዚህም እግዚአብሔር የአዳም ራስ መሆኑን፣ አዳምም የሴት ራስ መሆኑን በድርጊት አስረዳን፡፡ እንዲሁም በዚህ ሥርዓት ክርስቶስ የቤተ ክርስቲያን ራስ ሆነ፡፡ እንዲህም ሊል ሲፈልግ ቅዱስ ጳውሎስ “የወንድ ራስ ክርስቶስ፣ የሴት ራስ ወንድ፣ የክርስቶስም ራስ እግዚአብሔር” ብሎ ጻፈልን፡፡
ትንታኔው ይህን ከመሰለ እንግዲህ የራስ ተግባሩ ምንድን ነው? ብለን እንጠይቅ፡፡ ቀሪውን አካል በማስተዋል በሰከነ ግብታዊነት ባልተቀላቀለበት በጎ ሕሊና መምራት አይደለምን? እነዚህ ተግባራት የማን ናቸው? የነፍስ ተግባር አይደሉምን? በነፍስ ተፈጥሮ ውስጥ ስሜታዊነት ቦታ የለውም፡፡ ስለዚህ ወንድ ልጅ የነፍስን ሥፍራ ይዞ ቤቱን ይመራል፡፡ ሴትም የሥጋን ሥፍራ ይዛ የነፍስን ፈቃድ ተረድታ በሁሉ ቤተ ክርስቲያንን መስላ ለባልዋ ትታዘዛለች፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ይህን አስመልክቶ “ዳሩ ግን ቤተ ክርስቲያን ለክርስቶስ እንደምትገዛ እንዲሁ ሚስቶች ደግሞ በሁሉ ለባሎቻቸው ይገዙ”(ኤፌ.5፡24) ብሎ አስተማረ፡፡
ይህን መሠረት አድርጎ አምብሮስ ሔዋን ማለት ስሜት አዳም ማለት አእምሮ ማለት ነው ብሎ ጽንሰ ሃሳባዊ ትርጉም(contextual meaning) ሰጥቶ እናገኛለን፡፡ ቅዱሳን የሶርያ አባቶች ደግሞ ነፍስን በወንድ ሴት ልጅን በሥጋ መስለው ያስተምራሉ፡፡  እንዲህ ሲባል የሥራ ድርሻውን ለመግለጽ እንጂ ሴት ልጅ አእምሮ የላትም ወንድ ልጅ ደግሞ ስሜት የለውም ማለት አይደለም፡፡ እንዲህ ማለትም ከእኛ ይራቅ፡፡ ሥጋም ነፍስም በክርስቶስ አምላክ ሆነዋል፡፡ ሁለቱም ከብረዋል ሁለቱም ነግሠዋል፡፡ ስለዚህ የወንድ ራስነት ተፈጥሮአዊ ነው እንጂ በጊዜ ሂደት የተከሰተ አይደለም፡፡
ነገር ግን እግዚአብሔር በደገኛ ሕጉ ለእኛ የሰጠንን ሥርዓት ራሳችንን እንደምናውቀው አውቀን እንተገብረው ዘንድ የሠራው ነው፡፡ እርሱ ለቃሉ ታማኝ ነው፡፡ ከሕግ አንዲት የውጣ ከምትጠፋ ሰማይና ምድር ብታልፍ ይቀላል ብሎ አሰተምሮናልና፡፡ ጌታችንም አንድ ናቸው እንጂ ወደፊት ሁለት አይደሉም እንዲል በባልና ሚስት ያለው አንድነት በእርግጥ የነፍስና የሥጋ ተዋሕዶ አምሳል ነው፡፡ ነፍስን እና ሥጋን ሞት እንጂ ሌላ እንደማይለያቸው እንዲሁ ባልና ሚስትን ሞት እንጂ ሰው እንዳይለያቸው ጌታችን አስተምሮአል፡፡ ይህ የአምላክ የማይለወጥ ፈቃዱ ነው፡፡
የሆነ ሆነና ወዳጆቼ አንዳንዴ ባለማስተዋል ብትፈጸም “አይቶ የተመኘ አመነዘረ” እንዲል ዘማ የምታደርግ በማስተዋልና እግዚአብሔርን በማወቅ ሆነው ቢያገኟት የአምላክ ምርቃት የሆነችው በውስጣችን በተፈጥሮ ተተክላ ያለችው እውነተኛ ፍቅር አለች፡፡ ይህች ፍቅር አንድ ሰው ለአካለ መጠን ሲደርስ በውስጡ የምትቀጣጠል ስትሆን አንዷ የነፍስ ባሕርይ ናት፡፡ እናም አንድ ሰው በእውነተኛ ፍቅር የሚማረከው በነፍስ ውበቷ ተማርኮ ነው፡፡ ይህንን ግን በእርጅና ወይም በሕመም ወይም በጉዳት ጊዜ የሚያስተውሉት እንጂ በአንዴ የሚደርሱበት አይደለም፡፡ ነፍስ በተፈጥሮዋ አታረጅም ፤ አንድ በእውነተኛ ፍቅር የተየዘ ሰው የሚያፈቅራት ሴት ምንም ዓይነት አካላዊ ጉዳት ወይም ጉድለት ቢደርስባት ለእርሷ ያለው ፍጹም ፍቅር ፈጽሞ አይቀንስም፡፡ ምክንያቱም በሥጋ መስታወትነት ያፈቀረው ነፍሷን እንጂ ሥጋዋን አይደለምና፡፡ ቢሆንም የነፍስ ማኅደር የሆነውን አካሏን አይወደውም ማለት ግን አይደለም፡፡ በነፍስ ምክንያት ይወዳታል፡፡ ይህ በእርጅና እንኳ የማይቀዘቅዝ ፍቅር ይሆናል፡፡ በትንሣኤ ደግሞ የሥጋ ፈቃዱ ይጠፋና ፍጹም በሆነ መንፈሳዊ መዋደድ በእግዚአብሔር መንግሥት ይኖራሉ፡፡
ዘማ ሰው ግን ሥጋን ይመለከታል፡፡ ነገር ግን ያ የተማረከበት አካል ሲጎሰቁል፣ ሲታመም ሲያረጅ ሲደኸይ ከዚያ ፈጥኖ ይሸሻል፡፡ እናም ወዳጆቼ እንዳይቀላቀሉብን እንጠንቀቅ፡፡ ፍቅራችን ከምን እንደሆነ እናስተውለው የሥጋን ውበት ተመልክተን ከሆነ ለዝሙት መዳረጋችን አይቀሬ ነው፡፡ ይህም ነው “አይቶ የተመኘ አመነዘረ” ማለት፡፡ እግዚአብሔር የነፍስ ዓይናችንን ገልጦ የምንወዳትን እንስኪሰጠን ድረስ አላፊ ጠፊ ነውና በሥጋ ውበት አንማረክ፡፡ ይልቅ በሥጋ መቅደስ ውስጥ ያለችውን ነፍስን እንመልከታት፡፡ ያኔ የትዳር አጋራችንን ያለምንም የሥጋ ፍትወት ለይተን ማወቅ ይቻለናል፡፡

No comments:

Post a Comment