Saturday, June 1, 2013

በድዳና ደንቆሮው ሰው ስለ ሥነ- ተፈጥሮ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
24/09/2005
“ስብከት ወተግሣጽ ዘቅዱስ ኤፍሬም” ከተባለ መጽሐፌ የተወሰደ
እናንተ እውራን ሆይ ኑ ቅረቡ ያለዋጋ ብርሃንን ተቀበሉ ፡፡ እናንተ እግራችሁ የሰለለ ኑና በጌታ ተፈወሱ፤ አንተ ድዳና ደንቆሮ ናና ቃልን ከአምላክህ ተቀበል”
 በእጆቹ ጣቶች ጌታ የፈወሰው ያ ድዳና ደንቆሮ ሰው አምላክ ወደ እርሱ ቀርቦ ምላሱን እንደፈታለት ፣ ጆሮውንም እንደ ከፈተለት ተረድቶ ነበር፡፡(ማር.፯፥፴፩-፴፯) ምላሱ ረቶ እንዲናገር ፣ ጆሮውም እንዲሰማ  የጌታ ጣቶች ባይነኩት ኖሮ መለኮት እንደነካው ባልተረዳ ነበር ፡፡ ነገር ግን በጣቶቹ መለኮት የምላሱን እስራት ፈታ የጆሮዎቹን በሮች ከፈተ፡፡
ሰውነታችን ፈጣሪ የሆነው እርሱ ወደ ሕመምተኛው ቀረበ ግሩም በሆነው ድምፁ ያለአንዳች ሕመም የጆሮዎቹን መስኮቶች ከፈታው፡፡ አንደበቱ ቃልን ከመውለድ መክኖ የነበረውን ይህን ድዳ ሰው የምስጋናን ቃል እንዲወልድ በማድረግ የቃል መካንነቱን አራቀለት፡፡ አዳምን ሲፈጥረው ያለ አንዳች ትምህርት እንዲናገር እንዳደረገው፤ እንዲሁ ይህንንም ድዳና ደንቆሮ የነበረውንም ሰው ተምሮ ለማወቅ አስቸጋሪ የሆነውን ቋንቋ በአንዴ እንዲናገር አበቃው፡፡

አነሆ ሌላ ጥያቄ የሚያስነሣ ጉዳይ በዚህ ግልጽ ሆ፡፡ የትኛውን ቋንቋ ነው ድዳና ደንቆሮ የነበረው ሰው የተናገረው? ብለን ብንጠይቅ ለዚህ ጥያቄ መልስ ማግኘት ቀላል ነው፡፡ ነገር ግን ነፍሳችን ከዚህ የሚልቀውን እውቀት እንድንፈልግ ታነሣሣናለች፡፡ ይህም እውቀት ለድዳው ሰው በተፈጸመለት ተአምራት መነሻነት የአዳምም ፈጣሪ እርሱ እንደሆነ ያረጋግጥልናል፡፡
ከዚህ እውነታ ተነሥተን የአዳም ልጅ የሆነውን ይህን ሰው ይናገር ዘንድ ያበቃው እርሱ ለአዳምም ቋንቋን የሰጠው እርሱ እንደነበረ እንገነዘባለን፡፡ ጌታችን በዚህ ቦታ የተጓደለ ተፈጥሮን እንዲሟላ ከማድረጉ የተነሣ እርሱ አስቀድሞም የሰውን ተፈጥሮ አሟልቶ የፈጠረ ፈጣሪ መሆኑን አስረዳን፡፡
ከፍጥረት ሁሉ የምንልቅበት የኛ የሰዎች ተፈጥሮ መናገር መቻላችን ነው፡፡ ከዚህ ተነሥተን ድዳ መሆን ከጉድለቶች ሁሉ ትልቁ ጉድለት መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ በዚህም ድዳና ደንቆሮ የነበረውን ሰው በመፈወሱ ጉድለቶችን መሙላት ለእርሱ እንደሚቻለው ገለጠልን፡፡ ከማኅፀን እያንዳንዱን የአካል ክፍል አሟልቶ በሕቡዕ የሚፈጥር እርሱ እንደሆነ እንረዳ ዘንድ የዚህን ሰው ጉድለቶች በግልጽ ሞላለት፡፡ በዚህም ፍጥረታት ሁሉ በእርሱ እንደተፈጠሩ ግልጽ ሆነ፡፡
 ጌታችን በጣቶቹ ላይ ምራቁን እንትፍ ብሎ ደንቆሮ በሆነው ጆሮ ውስጥ አስገባና ፈወሰው፡፡ በምራቁም አፈሩን ለውሶ ጭቃ በማድረግ እውር በሆነው ሰው ዐይን ላይ በመቀባት ዐይኖቹን አበራለት፡፡ ጌታችን ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ እውር የነበረውን ሰው የዐይኑን ኳስ ጉድለት እንደሞላለት ፣ በጆሮውም ጉድለት ያለበትን ሰው ጉድለቱን ሞልቶ እንደፈወሰው፣ እንዲሁ ሙሉ አካሉ ከሆነው ቅዱስ ሥጋውና ቅዱስ ደሙ የእኛ ትልቁ ጉድለታችን እንዲሞላ አወቅን ተረዳን፡፡
ነገር ግን የእኛን ጉድለት ይሞላ ዘንድ ለጌታ ከአካሉ ክፍል ቆርጦ መስጠት አላስፈልገውም፡፡ ልክ ሟች የሆንን ሰዎች ከምንመገበው ምግብ ባገኘው ኃይል ሰውነታችን እንዲበረታ ጉድለታችንም እንዲሞላ፤ እንዲሁ ከቅዱስ ሥጋውና ደሙ  በመነጨው መለኮታዊ ኃይል ጉድለታችን ይሞላል፡፡ ጌታችን ለሙታን ነፍሳቸውን መልሶ በሕይወት አንዲመላለሱ የሚያደርግ ከሆነ ፤ በአካሉ(በቅዱስ ሥጋውና ደሙ) ሙታነ ነፍስ ጉድለታቸው ተሟልቶ በሕይወት እንዲመላለሱ እንዴት አያደር ይሆን !
 ነቢያት ሌሎች ተአምራትን ፈጸሙ ፡፡ ነገር ግን ከእነርሱ መካከል አንድም ነቢይ በአካሉ የአካል ሕዋሳትን ጎድለት የሞላ የለም፡፡ ይህም የአካል ክፍሎችን ጉድለት መሙላት የእግዚአብሔር ድርሻ እንደሆነ ያስረዳናል፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት የአካል ጉድለቶችን መሙላት በእርሱ ብቻ የሚፈጸም አምላካዊ ተግባር እንደሆነ ነፍሳችን ትረዳው ዘንድ ነው ፡፡
 የፍጥረትን ጉድለት ሊሞላ የሚችለው የፍጥረት አስገኚ የሆነ ፈጣሪ ብቻ እንደሆነ እውነተኛ የሆነ ሰው ሁሉ ይረዳ፡፡ ጌታችን ከዕርገቱ በኋላ ሐዋርያት በልዩ ልዩ ልሳናት እንዲናገሩ ማድረግ እንደሚቻለው ያስረዳ ዘንድ በምድር ሳለ ድዳና ደንቆሮ ለሆነው መስማትንና ያልተማረውን ቋንቋ መናገርን ሰጠው ፡፡
ጌታችንን የሰቀሉት ወገኖች እርሱን ገድለው ከቀበሩት በኋላ በእርሱ ይፈጸሙ የነበሩ ተአምራ በሙሉ አብረው የሚቀበሩ መስሎአቸው ነበር፡፡ ነገር ግን የተአምራ ባለቤት ሕያው እንደሆነ ይረዱ ዘንድ በእርሱ ይፈጸሙ የነበሩት ተአምራ በሐዋርያት በኩል መፈጸማቸውን ቀጠሉ ፡፡
 እነዚህ ወገኖች አስቀድመው “ደቀመዛሙርቱ መጥተው ሰረቁት” በማለት የጌታን ትንሣኤ ለመደበቅ የሞከሩ ነበሩ፡፡ ነገር ግን የጌታችን ተአምራ በሐዋርያት በኩል ሲፈጸሙ በተመለከቱ ጊዜ በፍርሃት ራዱ ፡፡ ክርስቶስን ከመቃብር ሰርቀውታል” የተባሉት ደቀመዛሙርቱ ሙታንን ሲያስነሡ ተገኙ፡፡ ኃጢአተኞች ግን በፍርሃት የእርሱን ትንሣኤ ለመደበቅ ሲሉ “ደቀመዛሙርቱ መጥተው ሥጋውን ሰረቁት” ብለው ዋሹ፡፡ ጠባቂዎች አንቀላፍተው ሳሉ ሥጋውን ከመቃብር ሰረቁ” የተባሉት ሐዋርያት ግን ሞት የሕያዋን ሁሉ ሕይወት የሆነውን ይዞ ማስቀረት እንደማይቻለው ሊያስገነዝቡ ሰረቃችሁት በተባሉት ክርስቶስ ስም ሞትን ሲያስጨንቁት ተገኙ፡፡
ስለዚህም ከስቅለቱ ፊት ለደንቆሮው የመስማት ኃይልን የሰጠ ፣ ከስቅለቱ በኋላ ሁሉንም ጆሮዎች ትንሣኤውን ሰምተው ያምኑ ዘንድ ከፈታቸው፡፡ እኛ ቃሉን መስማታችን በእርሱ ፈቃድ እንደሆነ ይታወቅ ዘንድ ደንቆሮና ድዳ በሆነው ሰው አስረዳን ፣ እንዲሁ የእኛ አንደበት ለስብከት መከፈቱም በእርሱ እንደሆነ በዚህ ድዳ ሰው ገለጠልን፡፡

1 comment:

  1. እነዚህ ወገኖች አስቀድመው “ደቀመዛሙርቱ መጥተው ሰረቁት” በማለት የጌታን ትንሣኤ ለመደበቅ የሞከሩ ነበሩ፡፡ ነገር ግን የጌታችን ተአምራት በሐዋርያት በኩል ሲፈጸሙ በተመለከቱ ጊዜ በፍርሃት ራዱ ፡፡ “ክርስቶስን ከመቃብር ሰርቀውታል” የተባሉት ደቀመዛሙርቱ ሙታንን ሲያስነሡ ተገኙ፡፡ ኃጢአተኞች ግን በፍርሃት የእርሱን ትንሣኤ ለመደበቅ ሲሉ “ደቀመዛሙርቱ መጥተው ሥጋውን ሰረቁት” ብለው ዋሹ፡፡ “ጠባቂዎች አንቀላፍተው ሳሉ ሥጋውን ከመቃብር ሰረቁ” የተባሉት ሐዋርያት ግን ሞት የሕያዋን ሁሉ ሕይወት የሆነውን ይዞ ማስቀረት እንደማይቻለው ሊያስገነዝቡ ሰረቃችሁት በተባሉት ክርስቶስ ስም ሞትን ሲያስጨንቁት ተገኙ፡፡

    ReplyDelete