Friday, March 30, 2012

የመንፈስ ቅዱስ እናትነት



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
22/07/2004
የክርስቶስ ልብ የተባለ፤ የእግዚአብሔር አብ እስትንፋሱ እንዲሁም የፍጥረት ሁሉ አስገኚ የሆነው መንፈስ ቅዱስ ለእኛ ለተጠማቂያን ክርስቲያኖች እናታችን ነው፡፡ እርሱ የእግዚአብሔር ብቸኛ ልጁ የሆነውን አፍቃሪያችንን ክርስቶስ ኢየሱስን  ይበልጥ እንድናውቀውና እንድንረዳው እንዲሁም እርሱን አብነት አድርገ እርሱ የሞተለትን የሰውን ልጅ ለእግዚአብሔር አብ እንድንማርክና የእግዚአብሔር አብና የእግዚአብሔር ወልድ ልጆች፣ የክርስቶስ ወንድሞች(በጸጋ) በማድረግ እንድናቀርባቸው፤ በጥምቀት ካህናት፤ የክርስቶስ ወታደሮች፤ የእርሱ አባሳደሮች አድርጎ የሾመን ነው፡፡ ስንጠመቅ ለእያንዳንዳችን ራሱ በሰጠን ጸጋ እንደ እናት ሰብስቦ የጸጋውን ወተት የሚመግበን፣ በእርሱም ባገኘነው ክርስቶስን በሚመስል ተፈጥሮአችን በአእምሮም በአካልም በሞገስም ልክ እንደ እናት እቅፍ ድግፍ አድርጎ በፍቅር የሚያሳድገን እርሱ ነው፡፡


በውስጣችን አድሮ የእግዚአብሔርን እውቀት የሚገልጥልን፤ የእርሱ የሆነውን የሚለይልን፤ የሚቀድሰን በቅዱሳን መላእክትም ጉባኤም እንድንገኝ የሚያበቃን፤ ከዚህም ባለፈ እሺ ካልነውና ከሰማነው በአብ ቀኝ የሚያቆመን  እርሱ ነው፡፡ እርሱን እናዳምጠውና ድምፁንም እንድንለይ አስቀድሞ በጥምቀት የሚበሰብሰውን ምድራዊ አካል ገፍፎ የማይበሰብስ ሰማያዊ አካል አለበሰን፡፡ በዚህ አዲስና መንፈሳዊ ተፈጥሮአችን በኩል የእግዚአብሔር መንፈስ እኛን ይነጋገረነናል፡፡ እኛም እርሱን እናዳምጠዋለን፡፡ እንዲህ ሲባል ግን እግዚአብሔር አብና እግዚአብሔር ወልድንም ከእኛ ጋር አይነጋገሩም ማለት አይደለም፡፡ 
እርሱ በእኛ በጎ ምግባር ደስ ከተሰኘ በእኛ ሰውነት በኩል ታላላቅ ተአምራትንና ምልክቶችን ያደርጋል፡፡ ከእግዚአብሔር የሚሰወር አንዳችም እውቀት እንደሌለ ሁሉ እኛም ከእርሱ ጋር ነንና ከእኛ የሚሰወር ወይም የሚጸነን አንዳችም ዓለማዊውም ሆነ መንፈሳዊ እውቀት አይኖርም፡፡ የምድራዊውን እውቀት ድንቁርና የሚያሰኘው መንፈስ ቅዱስ በእኛ ውስጥ ሆኖና  ከልባችን ይልቅ ወደእኛ ቀርቦ ሳለ እንዴት ምድራዊው እውቀት ሊከብደን፣ መንፈሳዊው ጥበብ ሊሰወረን ይችላል?
ሁሉ በእርሱ ተሰጥቶናል፡፡ እርሱ መንፈስ ቅዱስ በሰጠን መንፈሳዊ ጸጋዎች በፍቅር በመሆን ከተጋን ክርስቶስ ኢየሱስ በእኛ ተገልጦ ሳኦልን በደማስቆ ጎዳና ስለክርስቲያኖች እንደተዋጋው እንዲሁ እኛን ሊያሳድዱ ከተነሡት ጋር በመለኮታዊው ግርማው ተገልጦ ይወጋልናል፡፡ እርሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሳኦልን “ስለምን ታሳድደኛለህ” ብሎ በመገሠጽ ክርስቲያኖችን “እኔ” ሲላቸው አላፈረም፡፡ሰለዚህም አጋንንት በእኛ ፊት ጸንተው መቆም አይቻላቸውም፡፡ በሰው አእምሮ ውስጥ የሚመላለሰውን አሳብ በእርሱ ማወቅ ይቻለናል፡፡ የሰውንም አእምሮ በቀላሉ ልንማርክ፤ የጠላት የዲያብሎስንም ምሽጎችንም ልናፈራርሳቸው ይቻለናል፡፡ እንዲህ የሚሆንልን ግን መንፈስ ቅዱስ በእኛ በጎ ሥነምግባር ደስ የተሰኘ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡  
በመንፈስ ቅዱስ እናትነት ሥር ካለን ሁሉ የእኛ ነው፡፡ ራስ እንጂ ጅራት አንሆንም፡፡ ነገር ግን ለአእምሮአችን ማስተዋልን የሚሰጠውን መንፈስ ቅዱስን ልናውቀውና ልንታዘዘው ይገባናል፡፡ ይህንን ልንረዳ የምንችለው ግን በጸሎትና በጾም የተጋን እንደሆነ ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለዚህ ሲያስተምር “ትጉና ጸልዩ መንፈስስ ተዘጋጅታለች ሥጋ ግን ደካማ ነው”አለን፡፡ እንዲህ ሲባል ልክ እንደ ኤልሳቤጥ በውስጣችሁ ያደረው መንፈስ ቅዱስ ምሥጢሩን ይገልጥላችኋል ሲለን ነው እንጂ ስንተጋ የሚቀርበን ስንሰንፍ የሚርቀን ሆኖ አይደለም፡፡ በእነዚህና በሌሎችም መንፈሳዊ የትሩፋት ሥራዎች ምክንያት መንፈስ ቅዱስ ለአንደበታችን የምናገረውን ሲያቀብለን፣ የምንሠራውን ሲያቀናልን፣ የምንበላውን ሲባርክልን፣ በሰው ፊትም ሞገስን ሲሰጠን፤ ለአእምሮአችን ማስተዋለን ሲያበዛልን እናገኘዋለን፡፡ በውስጣቸን ከትሞ ያለውን መንፈስ ቅዱስን ስለምናውቀውም እናናግረዋለን፤ ከእርሱም መጽናናትን እናገኛለን፤ በእርሱም ለኢአማንያን በበጎ ሥራዎቻችን እንደ ብርሃን በመታየት እነርሱን ለእግዚአብሔር እንማርካለን፡፡ እኔ ይህን ያህል ካልኩ የሶርያ ቅዱሳን አባቶች ስለመንፈስ ቅዱስ እናትነት ምን እንደሚሉ ደግሞ ከዚህ በታች ያለውን ጽሑፍ እናንበበው፡፡  
“የርግቢቱ ክንፎች  በጫጩቶቿ ላይ ረበው እንዲገኙ፤
የጫጩቶቹዋም መንቁሮች ወደ እርሱዋ መንቁር አንጋጠው እንዲመለከቱ፤
 እንዲሁ የመንፈስ ቅዱስ ክንፎችም በአእምሮዬ ላይ ረበው ይገኛሉ፤
በእርሱዋም ያለመቋረጥ በመታደሴ ምክንያት በእናቱ ማኀፀን ሳለ የጌታውን እናት ድምፅ በመስማቱ በደስታ እንደ ዘለለው መጥምቁ ዮሐንስ በደስታ ዘለልኩ፡፡”  
በሌላ ስፍራ ላይ ደግሞ
“በጽዋ ለእኔ ወተት ቀረበልኝ፤
በጌታዬ ርኅራኄ ጣፍጦኝ  ጠጣሁት፤
ጽዋው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤
አስቀድሞ ለልጆቹ ከወተቱ ይመግባቸው የነበረው እግዚአብሔር አብ ነው፡፡
ወተቱንም እንዲሰጥ የምታደርገው መንፈስ ቅዱስ ናት፤
የመንፈስ ቅዱስ ጡቶች በወተት የተሞሉ ነበሩ፤
ነገር ግን የሰው ልጆች የእግዚአብሔር ልጅነትን ሥልጣን ሳያገኙ መመገብ የሚገባቸው አልነበረምና፣
መንፈስ ቅዱስ በውስጡዋ ሥፍራን አዘጋጀችላቸው፤
የእግዚአብሔር አብን ሁለቱን ጡቶች(ብሉይ ኪዳንና ሐዲስ ኪዳንን) በአንድ ላይ ደባለቀች፤
በእርሱዋ ካልሆነ በቀር በክርስቶስ ያመኑት እርሱን ስለማይረዱትና በአብ ቀኝ መቆምንም ስለማያገኙ፤
 ከጡቶቹዋ ወተት ትመግባቸው ዘንድ ከቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ተገኘች፤
ድንግልንም እግዚአብሔር ቃልን በሥጋ ፀንሳ ለመውለድ እንድትበቃ አደርገቻት፤
በእርሱዋም ምክንያት ታላቅ በሆነ በጌታ ርኅራኄ፣ ቅድስት ማርያም ድንግልናን ከእናትነት ጋር አስተባብራ ተገኘች፡፡”(ማኀልየ ማኅልይ ዘሶርያ)  



3 comments:

  1. “የርግቢቱ ክንፎች በጫጩቶቿ ላይ ረበው እንዲገኙ፤
    የጫጩቶቹዋም መንቁሮች ወደ እርሱዋ መንቁር አንጋጠው እንዲመለከቱ፤
    እንዲሁ የመንፈስ ቅዱስ ክንፎችም በአእምሮዬ ላይ ረበው ይገኛሉ፤
    በእርሱዋም ያለመቋረጥ በመታደሴ ምክንያት በእናቱ ማኀፀን ሳለ የጌታውን እናት ድምፅ በመስማቱ በደስታ እንደ ዘለለው መጥምቁ ዮሐንስ በደስታ ዘለልኩ፡፡”

    ReplyDelete
  2. የመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስነቱ ለእግዚአብሔር አብ ብቻ መስሎ ቀርቧል ለእግዚአብሄር ወልድም ነውና እንደአባቶች ጨርሶ ቢነገር። አብ የስላሴ ልብ፣ ወልድ የስላሴ ቃል፣ መንፈስ ቅዱስ የስላሴ እስትንፋስ።

    ReplyDelete
  3. መንፈስ ቅዱስ ከቅድስት ሥላሴ አንዱ ሲሆን ከአብ የሰረጸ ከአብና ከወልድ ጋር በመለኮት
    በስልጣን በአገዛዝ በመሳሰሉት እኩል ወይንም አንድ ነው። እንደ እግዚአብሔር አብ እና
    እንደ እግዚአብሔር ወልድ(ኢየሱስ ክርስቶስ) መንፈስ ቅዱስ በራሱ የተለየ አካልና ግብር
    አለው። ዮሐ.፲፭፥፳፮። መንፈስ ቅዱስ ከዘመናት አስቀድሞ ከአብና ከወልድ ጋር
    ዓለማትን የፈጠረ ነው። ቅዱስ ዳዊትም በመዝሙር ፴፪፥፮ ላይ ሲል ተናግሯል።
    መንፈስ ቅዱስ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ምድር የመጣበትን አላማ
    አበክሮ የሚገልጽና ጌታችንም ወደ ቀደመ ክብሩ በምስጋናና በእልልታ ካረገ በኋላ በ፲ኛው ቀን
    ለሐዋርያት ጸጋውን በማፍሰስ የተገለጸ የቤተክርስቲያን ጠባቂና መሪዋ፤ በእግዚአብሔር ልጅ
    ያመኑትንና በስሙ የተጠሩትን ክርስቲያኖች የሚያጽናና፣ በኃይማኖት በምግባርና በተጋድሎ
    የሚያጸና፣ ጥበብንና ማስተዋልንም የሚያድል ነው (ኢሣ.፲፩፥ ፪)። ክርስቲያኖች ከጌታ
    የተማሩትን መልካም የሆነውን የጽድቅ ሥራ እንዲሠሩ ዘወትር በልቦናቸው አድሮ የሚያሳስብ
    እርሱ መንፈስ ቅዱስ ነው። ዮሐ. ፲፬፥፳፮ በማለት
    ሐዋርያት/ክርስቲያኖች በሚሠሩት ሥራ ሁሉ መንፈስ ቅዱስ እንደማይለያቸው ጌታችን
    አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሯል።
    መንፈስ ቅዱስ በእምነት ጸንተው በጸሎት ለሚተጉ ክርስቲያኖች ሁሉ የሚሰጥ ኃብት ነው።
    በተለይም በአንድ ልብ ሆኖ በኅብረት በሚደረግ ጸሎት ምልጃና ጉባዔ መንፈስ ቅዱስ በቶሎ
    ይሰጣል/ይወርዳል/ይገኛል፤ ለሁሉም እንደ ችሎታውና እንደ አቅሙም ፀጋንና ስጦታን
    ያድላል። ሐዋ.ሥ. ፪፥ ፩-፬

    ReplyDelete