Wednesday, August 22, 2012

ትንሣኤሃ ለቅድስት ድንግል ማርያም



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
16/12/2004
በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ለሕዝቡ ሲገለጥ በቃል ኪዳኑ ታቦት ላይ በማደር የምስክሩን ድንኳን በክብሩ ደመና ይከድነው ነበር፡፡(ዘጸአ.40፡34-38) ንጉሥ ሰሎሞንም የእግዚአብሔርን ቤተመቅደስ ሠርቶ ከፈጸመና የቃል ኪዳኗን ታቦት ካስገባ በኋላ እግዚአብሔር በቃል ኪዳኗ ታቦት ላይ በማረፍ መቅደሱን በክብሩ ደመና ከድኖት ነበር፡፡(2ዜና.7፡2-4) እነዚህ የእናታችን የቅድሰት ድንግል ማርያምና የእኛ ምሳሌዎች ናቸው፡፡
ሰውን የሚወድ እግዚአብሔር የሰውን ልጅ  በመተላለፉ ምክንያት ተሰነካክሎ ወድቆ እንዲቀር ስላልወደደ እግዚአብሔር ቃል በራሱና በአባቱ እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ ሰብእናችንንም በራሱ ቀድሶና አንጽቶ ከራሱ ጋር ለማዋሐድና እኛን ቤተመቅደሱ ለማሰኘት ቅድስት እናታችንን ማደሪያ ታቦቱ ትሆን ዘንድ መረጣት፡፡ ከእርሱዋም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሱዋ ነፍስ በመንሳት ተፀንሶ ተወለደ፡፡ በዚህም በነቢዩ አሞጽ አድሮ“በዚያ ቀን የወደቀችውን የዳዊትን ድንኳን አነሣለሁ”(አሞ.9፡11) ብሎ የተናገረውን ቃል ከዳዊት ዘር ከሆነች ከቅድስት ድንግል ማርያም በመወለድ ድንኳን የተባለችውን ሰብእናችንን አከበራት፡፡


ይህም እንደተፈጸመ ለማጠየቅም መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ወደ ቅድሰት እናታችን በመምጣት “መንፈስ ቅዱስ ባንቺ ላይ ይመጣል የልዑልም ኃይል ይጸልልሻል”(ሉቃ.1፡35)በማለት ቅድስት ድንግል ማርያምን የምስራች አላት፡፡ በዚህም ቅድስት እናታችን ሰውነቱዋን የእግዚአብሔር ቃል ማደሪያ ታቦት በማድረግ ሰብእናችንን የጌታ ቤተመቅደሱና ማደሪያ ድንኳኑ እንዳደረገችው ለሁላችን የተረዳ ሆነ፡፡
ነገር ግን ነቢዩ ዳዊት ቅድሚያ ትንሣኤ የሚፈጸምለት መቅደሱና ድንኳኑ ለተባልነው ለእኛ ሳንሆን ማደሪያ ታቦቱ ለሆነችው ለቅድስት ድንግል ማርያም እንደሆነ አስቀድሞ “አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” ብሎ ጽፎልናል፡፡(መዝ.131፡8) ሰለዚህም ምክንያት ቅድስት እናታችን በ64 ዓመቱዋ ካረፈች በኋላ ልጇ ቅድስት የሆነችውን ሥጋዋን ክብርት ከሆነችው ነፍሷ ጋር በማዋሐድ በትንሣኤ ክብር ትንሣኤዋን በመፈጸም በእርሱ ቀኝ አቆማት፡፡ እንዲህም ስለሆነ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እርሱዋን አስመልክቶ “በሰማይም ያለው የእግዚአብሔር መቅደሰ ተከፈተ የኪዳኑም ታቦት ታየ” እንዲሁም “ታላቅ ምልክት በሰማይ ታየ ፀሐይን ተጎናጽፋ ጨረቃን ከእግሮቹዋ በታች ያላት በራስዋም ላይ የአሥራ ሁለት ከዋክብት አክሊል የሆኑላት ሴት ነበረች” ብሎ በተደጋጋሚ ጻፈልን፡፡(ራእይ.11፡19፤12፡1) በእነዚህ ኃይለ ቃላትም ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ እንደፈጸመላት እናረጋግጣለን፡፡ እርሱዋም "ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል" ማለቱዋ በትንሣኤዋ ከምታገኘው ልዩ የሆነ ክብርም ጭምር ነው፡፡ ምክንያቱም ለሌሎች ያልተፈጸመው ለእርሱዋ ተፈጽሞላታልና፡፡ እነሆ አሁን ቅድስት እናታችን በትንሣኤ ክብር ከእግዚአብሔር ቀኝ ቆማለች፡፡(መዝ.44፡9)
ስለዚህም ቅድስት እናታችን  ሰውና እግዚአብሔር እርቅን እንደፈጸሙ ጌታችንን መድኅኒታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በመውለድ አስቀድማ ምስክር እንደሆነችን እንዲሁ በትንሣኤዋም(Assumption) ትንሣኤ ሙታን ለሰው ልጆች ሁሉ እንደማይቀር እውነተኛዋ ማረጋገጫ ሆነች፡፡
 ከእርሱዋ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሱዋ ነፍስ በመንሳት እኛን ማደሪያ ቤተመቅደሶቹ ላደረገን ለጌታችን ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በእርሱም ለእግዚአብሔር አብና ለእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን!!!    

2 comments:

  1. ሰውን የሚውድ እግዚአብሔር የሰውን ልጅ በመተላለፉ ምክንያት ተሰነካክሎ ወድቆ እንዲቀር ስላልወደደ እግዚአብሔር ቃል በራሱና በአባቱ እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ ሰብእናችንንም በራሱ ቀድሶና አንጽቶ ከራሱ ጋር ለማዋሐድና እኛን ቤተመቅደሱ ለማሰኘት ቅድስት እናታችንን ማደሪያ ታቦቱ ትሆን ዘንድ መረጣት፡፡ ከእርሱዋም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሱዋ ነፍስ በመንሳት ተፀንሶ ተወለደ፡፡ በዚህም በነቢዩ አሞጽ አድሮ“በዚያ ቀን የወደቀችውን የዳዊትን ድንኳን አነሣለሁ”(አሞ.9፡11) ብሎ የተናገረውን ቃል ከዳዊት ዘር ከሆነች ከቅድስት ድንግል ማርያም በመወለድ ድንኳን የተባለችውን ሰብእናችንን አከበራት፡፡

    ReplyDelete
  2. waw kale hiwoten yasemaln shime bertaln enwedhaln yantew temarih yohannes neg

    ReplyDelete