Wednesday, February 1, 2012

ቤተክርስቲያን (በቅዱስ ቶማስ)

ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
23/05/2004
ቤተክስቲያኔ ብርሃን ለሆነው ጌታ ሴት ልጁ፤
ንጉሡ በመለኮታዊ ብርሃኑ የከደናት፤
ማስተዋልዋ ደስ የሚያሰኝና መራኪ፤
በመልካም ሥነ ምግባርም ሁሉ የተጌጠች፤
ልብሶቹዋ መልካም መዓዛ እንዳላቸው ውብ አበቦች የሆኑላት ናት፡፡
ከእርሱዋ በላይ ንጉሥ ተቀምጦባታል፤ ከሥሩ ያሉትንም ይመግባቸዋል፤
እውነት ከራሱዋ በላይ ነው ደስታንም ተጫምታለች፡፡
ከንፈሮቹዋም ለጌታ ምስጋናን ያወጡ ዘንድ ተከፍተዋል፤      
የልጁ አሥራ ሁለቱ ሐዋርያትና ሰባ ሁለቱ አርድእትም በዙሪያዎቹዋ ናቸው፤
አንደበቱዋም ካህኑ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ገልጦአት እንደሚገባባት መጋረጃ ናት፤
አንገቱዋ በጌታ ወደ ታነጸችው ሰማያዊቱ ኢየሩሳሌም መወጣጫ ድልድይ ናት፤
እልፍኙዋ በወይን ጠጅና መልካም መዓዛ ባለው የድኅነት ሽቱ የተሞላች ናት፤                                         
በመካከሉዋ ሁሉን ደስ የሚያሰኝ እምነት፣ ተስፋ፣ ፍቅር የተጨመሩበት ጽና አለ፤
በውስጡዋም ትሑታን እርሱዋን ለማገልገል በትጋት ይፋጠኑበታል፤
ወደ ጌታ ሰርግ የጠራቻቸው እንግዶቹዋም በዙሪያዋ ታድመዋል፤
ሕያዋን የሆኑ አገልጋዮቹዋም ከፊቱዋ ቀድመው የሙሽራውን መምጣት በጉጉት ይጠባበቃሉ፤                           
አሳላፊዎቹ በጌታቸው ፊት ለመቆም እንዲበቁ በሙሽራው የክብሩ ብርሃን የተሸለሙ ናቸው፡፡
ቤተ ክርስቲያን ማለት እኛ ነን፤ አገልጋይዋም ካህን ነፍሳችን ናት፤ መቅደሱም ሥጋችን ነው፡፡ በእርሱዋ ምሳሌ ምድራዊቱ ቤተክርስቲያን ታነጸች፡፡ ለምድራዊቱ ቤተክርስቲያን በነፍስ ቦታ ካህኑ አለ፡፡ በሥጋም ቦታ እኛ አለን፡፡ ካህኑ በራሱ ካህንም ቤተ መቅደስም ነው፡፡ ቤተ መቅደስነቱ ለክርስቶስ ነው፤ካህንነቱ ለእኛ ነው፡፡ እኛም ለካህኑና ለክርስቶስ ቤተመቅደሱ ነን፡፡ እርሱ እኛን በማገልገል ጌታውን ክርስቶስን ይመስለዋል፡፡ ነፍሳችን ደግሞ ቅዱስ ታደርገው ዘንድ ሥጋዋን እንደ ካህን ታገለግለዋለች፡፡ እኛና ካህኑ በጥምረት ፍጥረትን ወደ ፈጣሪ የምናቀርብ ካህናት ነን፡፡
 ይህቺ ምድራዊቱ ቤተ መቅደስ የመንፈሱ ዘለዓለማዊ ቤተመቅደስ በተባለችው ሰውነታችን ምሳሌ የታጸች ናት፡፡ ይህ ይታወቅ ዘንድ ጌታችን ከቅድስት እናታችን የነሣውን ሰውነት ቤተመቅደስ አለው፡፡ ወደ ጌታ ቤተመቅደስ የሚያገባንም ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ነው፡፡ በእርሱም ከመለኮቱ ተካፋዮች እንሆናለን፡፡ በሰማያት ያለችው በእጅ ያልተሠራች ቤተመቅደስ የተባለችው ጌታችን ከድንግል የነሣት ሰብእናው ናት፡፡ ከእርሱም ኅብረት ይኖረን ዘንድ በጥምቀት የአካሉ ሕዋሳት በመሆን ወደ ሰውነቱ ቤተ መቅደስ ገባን፡፡ በእርሱም አማልክት ተባልን፡፡ እንዲህ ለወደደንና ላከበረን ፈጣሪያችን ክብር ምስጋና ይሁን ለዘለዓለሙ አሜን!!

No comments:

Post a Comment