Tuesday, January 17, 2012

አንብቦተ መጽሐፍ በቅዱስ ኤፍሬም


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
08/05/2004
አዲስ አበባ

           ቅዱስ ኤፍሬም ስለአንብቦተ መጽሐፍ  ፖፕሊየስ ለሚባል ወዳጁ በጻፈው ደብዳቤው ላይ እንዲህ ብሎ እናገኘዋልን፡-
“ንጹሕ መስታወት የሆነውን የጌታችንን ቅዱስ ወንጌል በእጅህ መያዝን ስላልተውክ መልካምን አደረግህ ፡፡ በእርሱ መስታወትነት ማንም ምን መምሰል እንዳለበት ይረዳበታል ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን የሚያነቡ ወገኖች በዚያ ውስጥ ምስላቸውን ከማግኘታቸው በተጨማሪ የራሳቸውን ተፈጥሮ በማስተዋል ከነውር እንዲጠበቁትና በቅድስና ጸንተው ያለመለወጥ እንዲመላለሱ ይረዳቸዋል ፡፡ በሰውነታቸውም ላይ ነውር አይገኝም ፤ ከእድፍም የጸዱ ይሆናሉ ፡፡
በመስታወት ፊት ባለቀለም ቁስ ቢቆም እንደቀለሙ ዓይነት እንዲሁ መስታወቱ ይሆናል ፡፡ ነገር ግን የመስታወቱ  ባሕርይው አይቀየርም ፡፡ ነጭ የሆነ ቁስ በፊቱ ቢያቆሙ ያንኑ ነጭ ቁስ መልሶ ያሳየናል ፡፡ ጥቁር ቀለም ያለው ቁስ በፊቱ ቢቆም የጥቁረቱን መጠን ያሳየዋል ፡፡ ቀይ ከሆነም ቅላቱን ያሳየዋል ፡፡ ውብ ገጽታ ካለው ደግሞ ውብቱን ያሳየዋል ፡፡ መልከጥፉም ከሆኑ እንዲሁም ለዐይን ምን ያህል እንደሚያስቀይሙ ያሳያቸዋል ፡፡ እያንዳንዱን የሰውነታችንን ገጽታ በዚህ መስታወት ውስጥ እናየዋለን ፡፡

መልከ ጥፉዎች በዚህም በመጽሐፍት መስታወትነት ራሳቸውን ተመልክተው ስለመልከ ጥፉነታችው ራሳቸውን ይገሥጻሉ ፡ ስለዚህም ራሳቸውን ከጉድፍ ያጸዳሉ ፤ አስቀያሚ ሆነው እንዲታዩ ያበቃቸውን ቆሻሻ ያስወግዳሉ :: ለቆነጃጅቶችም ውበታቸውን ጠብቀው እንዲዘልቁና ቆሻሻም እንዳይነካቸው እንዲጠነቀቁ እንዲሁም ተፈጥሮአዊ ውበታቸው ላይ አክለው እንደ ምርጫቸው ራሳቸውን እንዲያስውቡ ያተጋቸዋል ፡፡
ምንም እንኳ መጽሐፍ ቅዱስ ቃል አውጥቶ ባይናገርም ፤ በፀጥታው አብዝቶ ይጮኸል ፡፡ እርሱን ሕይወት የሌለው ግዑዝ ነገር አድርገህ ብትቆጥረውም ፤ጽድቅን ያውጃል ፡፡ የማይንቀሳቀስ ቢሆንም በደስታ ይቦርቃል ፡፡ ምንም እንኳ ሥጋን የለበሰ ባይሆን ማኅፀኑ እጅግ የከበረ በውስጡም ልዩ ልዩ እልፍኞች ያሉት ነው ፤ እያንዳንዱም የአካል ክፍል በውስጡ ይሠራል ፡፡ የእያንዳንዱ የአካል ቅርፅ ክፍልፋዮች በቅጽበት ይበጃጃሉ ፤ በእርሱ ውስጥ በማይታመን ፍጥነትም ይፈጠራሉ ፡፡
ይህ መስታወት በክርስቶስና በሐዋርያት ለሚሰበከው ወንጌል ምስል ነው ፡፡ በውስጡ በእርሱ ውበታቸውን የሚመለከቱበት መስታወት ይገኛል ፡፡ በእርሱም መልከጥፉዎች ነውራቸውን እንዲያዩ ስለሚሆኑ ስለመልከጥፉነታቸው ይገሠጻሉ ፡፡ ይህ መስታወት ልክ እንደ ተፈጥሮአዊ መስታወት ነው ፡፡ ነገር ግን የወንጌል ምስል ነው ፡፡ በሐዋርያት የተሰበከው ወንጌልም ከምስሉ(ከመጽሐፉ) ይልቅ ከላቀው ከማይጠፋው ከእርሱ የተገኘ ነው ፡፡ በእርሱ የፍጥረት መተላለፍ ሁሉ ይገሠጻል ፡፡
በእርሱም ራሳቸውን በኃጢአት ጭቃ ሳያሳድፉ ለጸኑት ክብርን ያጎናጽፋል ፡፡ በዚህ መስታወት ራሱን የሚመለከት ኃጢአቱን ይረዳል ፡፡ ይህንን የተረዳ ሰው ስለራሱ በጎነት ወይም መተላለፍ ስለሚያቅ ራሱን አስተካከሎ መምራትን ያውቃል ፡፡በዚያ ውስጥ ዐይኖቻቸው ንጹሐን የሆኑላቸው ወገኖች መንግሥተ ሰማያትት በውስጡዋ ተስላ ያገኙዋታል ፡፡ በእርሱ ውስጥ ያለው የእግዚአብሔር መልካሙ ስጦታ ጎልቶ ይታያል ፡፡ በዚያ ውስጥ መካከለኛ የተባለው የክርስቶስ ክብር ከፍታ ይታያል ፡፡ በዚህ እግዚአብሔር ለቅዱሳኖች ያዘጋጃቸው ማደሪያዎች እንዳሉ ማረጋገጥ ይቻላል ፡፡ በዚህ ውስጥም በገነት ያለው ተድላ ደስታ በግልጽ ይታያል ፡፡”

No comments:

Post a Comment