Monday, January 16, 2012

በእውን ሰው በመበደሉ መንፈስ ቅዱስ ይለየዋልን?




ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
 07/04/2004 ዓ.ም
አዲስ አበባ
መግቢያ
 ፊሊክስዩስ በሰሜናዊ ሶርያ ለምትገኝ ማቡግ ለምትባል ቤተክርስቲያን ጳጳስ የነበረ አባት ሲሆን ፤ በዘመኑ በጣም ታዋቂ የሆነ የነገረ-መለኮት ሊቅ ነበር፡፡ የኬልቄዶንን ጉባኤ በመቃወም በሶርያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ተጠቃሽ የሆነ አባት ሲሆን እርሱ የኬልቄዶንን ጉባኤን የመቃወሙ ምክንያት የኬልቄዶናውያን አስተምሀሮ መለኮትን ከትስብእት ለመነጣጠልና ለመለያየት የሚሞክር ትምህርት ነው በማለት ነበር፡፡ አብዛኛዎቹ የእርሱ ጽሑፎች በነገረ መለኮት ላይ ያተኮሩ ቢሆኑም የሥነ ምግባር ትምህርቶችንም አብዝቶ ጽፎልናል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አንዱ ይህን ይመስላል፡፡
“ከእግዚአብሐር የተቀበልነው መንፈስ ቅዱስ የነፍሳችን ነፍስ ነው፡፡ ስለዚህም  ጌታችን በሐዋርያት ላይ እፍ በማለት መንፈስ ቅዱስን አሳደረባቸው፡፡ በእነርሱም መንፈስ ቅዱስ የነፍሳችን ነፍስ ይሆን ዘንድ ለእኛ ተሰጠ፡፡ በተፈጥሮአዊዋ ነፍስ ነፍስ ይሆን ዘንድ መንፈስ ቅዱስን ተቀበልን፡፡ ልክ ነፍሳችን የሥጋችን ሕይወት እንደሆነች፤ መንፈስ ቅዱስም የነፍሳችን ሕይወት ማድረግ እንደሚገባን ለማስገንዘብ ለነፍሳችን ነፍስ ይሆን ዘንድ በጥምቀት መንፈስ ቅዱስን ተቀበልን፡፡ ከአዳም የተሰጠችው ሕይወት ከእግዚአብሔር እስትንፋስ የተገኘች ነበረች፡፡ “የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት” ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ ይህም መንፈስ ቅዱስ ነበር፡፡ ነገር ግን በመተላለፈ ከእርሱ ተወሰደ፡፡(ዘፍ.፪፥፯)

በአዲስ ኪዳንም ጌታችን በደቀመዛሙርቱ ላይ እፍ በማለት “መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ፡፡ ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል”(ዮሐ.፳፥፳፩-፳፪) በማለት መንፈስ ቅዱስን በሐዋርያት ላይ አሳደረባቸው፡፡ እንዴት ታዲያ የኃጢአትን ስርየት የሚሰጠው መንፈስ ቅዱስ በኃጢአት ምክንያት ከእኛ ይርቃል ልንል እንችላለን ? መንፈስ ቅዱስ ባለበት ኃጢአት ይርቃል ይባላል እንጂ መንፈስ ቅዱስ ከኃጢአት ፊት ይሸሻል ብሎ በመንፈስ ቅዱስ ላይ መናገር ተገቢ አይደለም፡፡ በብርሃን ፊት ጨለማ እንጂ በጨለማ ፊት ብርሃንን አይሸሽም፡፡ እንዲሁ ከኃጢአት ፊት መንፈስ ቅዱስ አይሸሽም የሚሸሸው ኃጢአት ነው እንጂ፡፡ ይልቅኑ እግዚአብሔርን ካልካድነው መንፈስ ቅዱስ በሰውነታችን ውስጥ ይኖራል፡፡ ነገር ግን በኃጢአታችን ልናሳዝነው እንችላለን፡፡ ይህ ደግሞ ተገቢ አይደለም፡፡  ነገር ግን በኃጢአት ምክንያት መንፈስ ቅዱስ ከእኛ ይለያል የምንል ትክክል አይደለንም፡፡
 መንፈስ ቅዱስ ለነፍሳችን ነፍስ ከሆነ፣ እንዲህ እንዲሆንም እንደ ቀዳማዊው አዳም በንፍሃት የተሰጠን ከሆነ፤ ልክ ነፍሳችን ከሥጋችን በተለየች ጊዜ ሥጋችን እንድትሞት እንዲሁ መንፈስ ቅዱስ ከነፍሳችን ተለየ የምንል ከሆነ  ነፍሳችን እንደምትሞት ግልጽ ሊሆንልን ይገባል፡፡ ልክ ነፍሳችን ከሥጋችን ብትለይ ሥጋችን ፈርሶና በስብሶ እንዲቀር፣ በሕይወትም ዳግም አንዲኖር ምንም ዐይነት መድኃኒት እንደማይገኝለት እንዲሁ በንስሐ እርሱን ማደስ ፈጽሞ አይቻለም፡፡
የአንድ ሕመምተኛ ዐይን አንዴ ከፈሰሰ ፈጽሞ አይድንም ፣ የተሰበረም እግር ወይንም የዞረ እጅ በመገጣጠሚያው ላይ በሚደርስበት ጉዳት የተነሣ ምንም በጨርቅ ብናስረው አንዴ ከአካሉ ከተለያየ ወይም ከሞተ ፈጽሞ ተመልሶ ሕያው አይሆንም፡፡ እነዚህ አካላት ሊድኑ የሚችሉት ያልጠፉ ወይም ፈጽሞ ከሌላኛው የአካል ክፍል ጋር ግንኘኙነታቸውን ያላቋረጡ ሕያዋን እንደሆኑ ብቻ ነው፡፡ እነዚህ አካላት ከዋናው አካል ጋር ፈጽመው ስለተለያዩ ግን ሕይወት አልባ ሆነዋል ፡፡ እንዲሁ መንፈስ ቅዱስ በኃጢአት ምክንያት ከነፍሳችን የተለየ እንደሆነ ነፍሳችን ያለጥርጥር ሞታለች፡፡ ስለዚህም ከኃጢአቷ ምንም ዐይነት ፈውስን የማግኘት እድሉ አይኖራትም፡፡ ምክንያቱም መንፈስ ቅዱስ በውስጡዋ የለምና፡፡ ሕይወቱን ላጣ ሰው መድኃኒት ወይም ለተቆረጠ አካል ማሰሪያ ጨርቅን ብንጠቀም ምን ይጠቅመዋል ? ሬሳ የሆነውን አካል የፈወሰ ዶክተር ታይቶ አይታወቅም ፤ ወይም አንዴ ተቆርጦ የሞተውን አካል በመግጠም እንደገና ሕይወት የዘራበት ሐኪም የለም፡፡ በነፍስም እንዲሁ ነው፡፡ በጥምቀት የተቀበልነው ለነፍሳችን ሕይወት የሆነው መንፈስ ቅዱስ ከተለየን ከነፍስ ሕመማችን መዳን አይቻለንም ፡፡ ስለኃጢአታችንም የምንገባው ንስሐ ምንም አይጠቅመንም፡፡
ከጥምቀት በፊት አንድ ሰው አሮጌው ሰው ይባል ነበር፡፡ (ኤፌ.፬፥፳፪) ነገር ግን ከጥምቀት በኋላ አዲሱ ሰው ተብሎ ተጠርቶአል፡፡(ኤፌ..፬፥፳፬) በተጠማቂው ሰውነት ውስጥ ያደረው መንፈስ ቅዱስ ለተጠማቂው አንደ ነፍስ ሆኖለታል፡፡ ስለዚህም መንፈስ ቅዱስ ለእርሱ ነፍስ ሆኖታል ማለት ነው፡፡ በእርሱ ውስጥ በጥምቀት ያደረው መንፈስ ቅዱስ እርሱን ሕያው አድርጎ ማኖሩ በዚህ ምድር ብቻ የሚቀጥል አይደለም ፤ ነፍሱ ከሥጋው ከተለየችም በኋላ ይህ ሰው ሕያው ሆኖ  ይቀጥላል፡፡
ስለዚህም ነው ቅዱሳን ከሥጋ ሞት በኋላ እንኳ  በእነርሱ ሰውነት ተአምራት ሲፈጸም የምናስተውለው ፡፡ ቅዱሳን ጻድቃን እና ሰማዕታት ምንም ተፈጥሮአዊቱ ነፍስ ከሥጋቸው ብትለይም ከእነርሱ ሰውነት መንፈስ ቅዱስ  አድሮ ስለሚገኝ አጋንንት በእነርሱ አስከሬን ፊት ጸንተው መቆም አይቻላቸውም፡፡ ወይም በእነርሱ አካል አድሮ በሚኖረው መንፈስ ቅዱስ ምክንያት ሲጮኽ ይስተዋላሉ፡፡ እንዲሁም በእነርሱ አፅም ተአምራት ሲፈጸም፣ ሕመምተኞችም ከሕመማቸው ሲፈወሱ እንመለከታለን፡፡
ከትንሣኤም በኋላ ነፍስ ወደ ማደሪያዋ ሥጋ ስትመለስ በእነርሱ ውስጥ መንፈስ ቅዱስ አድሮ ይኖራል፡፡ ከእነርሱ ፈጽሞ አይለይም፡፡ አንድ ሰው በጥምቀት መንፈስ ቅዱስን ከተቀበለ በኋላ ክህደትን ካልፈጸመ በቀር መንፈስ ቅዱስ ከእርሱ ፈጽሞ አይለይም፡፡ ትንሣኤአችንም በአካላችን ውስጥ ባለው መንፈስ ቅዱስ ተፈጽሞልናል ወይም በእርሱ ይፈጸመልናል፡፡  ስለዚህም ነው ጻድቃን ነፍሳቸው ከሥጋቸን ስትለይ አረፉ እንጂ ሞቱ የማንለው፡፡ ስለዚም ቅዱስ ጳውሎስ  “ወንድሞች ሆይ” ይልና “ተስፋ እንደሌላቸው እንደ ሌሎች ደግሞ እንዳታዝኑ አንቀላፍተው ስላሉት ታውቁ ዘንድ እንወዳለን”( ፩ተሰሎ. ፬፥፲፫)…” አለ፡፡
ለወደደን በልጁም ታላቅ በሆነ መጎብኘት የጎበኘን ለእግዚአብሔር አብና ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን፡፡ 

2 comments:

  1. ከትንሣኤም በኋላ ነፍስ ወደ ማደሪያዋ ሥጋ ስትመለስ በእነርሱ ውስጥ መንፈስ ቅዱስ አድሮ ይኖራል፡፡ ከእነርሱ ፈጽሞ አይለይም፡፡ አንድ ሰው በጥምቀት መንፈስ ቅዱስን ከተቀበለ በኋላ ክህደትን ካልፈጸመ በቀር መንፈስ ቅዱስ ከእርሱ ፈጽሞ አይለይም፡፡ ትንሣኤአችንም በአካላችን ውስጥ ባለው መንፈስ ቅዱስ ተፈጽሞልናል ወይም በእርሱ ይፈጸመልናል፡፡ ስለዚህም ነው ጻድቃን ነፍሳቸው ከሥጋቸን ስትለይ አረፉ እንጂ ሞቱ የማንለው፡፡ ስለዚም ቅዱስ ጳውሎስ “ወንድሞች ሆይ” ይልና “ተስፋ እንደሌላቸው እንደ ሌሎች ደግሞ እንዳታዝኑ አንቀላፍተው ስላሉት ታውቁ ዘንድ እንወዳለን”( ፩ተሰሎ. ፬፥፲፫)…” አለ፡፡
    ለወደደን በልጁም ታላቅ በሆነ መጎብኘት የጎበኘን ለእግዚአብሔር አብና ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

    ReplyDelete
  2. ACCORDING TO THE GOAL OF SALIVATION, IT IS DIFFICULT TO CONCLUDE THE HOLLY SPIRIT DETACHED FROM THE FLESH ETERNALLY AS THE FLESH BEING COMMITTED IN SIN.FLESH IS SIMPLY COLLECTION OF DUST WITH MIXED OF WATER, NOTHING MORE NOTHING LESS.IT IS THE SPIRIT PART OF THE BEING , THE SOUL OF THE PERSON MATTERS MOST IN CASE OF SALIVATION.BECAUSE OF THE VERY WEAK PART OF THE FLESH, 100S OF PROPHETS FIGHT FOR IT.THE FLOWER OF JESUS DO NOT AFRAID THOSE WHO KILL THEIR FLESH.THE PINT IS FEAR OF SIN THAT ABOLISHES OUR SOUL, THAT IS INSULTING THE HOLLY SPIRIT , DISTRACTING THE WORK OF GOD AND BEHAVING LIKE ANNANIYA WHO CHEAT THE HOLY SPIRIT.IF WE DO THESE, THE HOLLY SPIRIT TOTALLY DETACHED FROM US FOREVER, EVEN COULD NOT GET IT WITH REDEMPTION. ASSEGED G/MEDHIN.

    ReplyDelete