Saturday, July 28, 2012

“ሽሽታችሁ በክረምት ወይም በሰንበት አይሁን”(ትርጉም በቅዱስ ኤፍሬም)



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
21/11/2004 ዓ.ም
ተወዳጆች ሆይ ዛሬ ጌታችን “እንግዲህ በነቢዩ በዳንኤል የተባለውን የጥፋት ርኩሰት በተቀደሰችው ሥፍራ ቆሞ ስታዩ አንባቢው ያስተውል”(ማቴ.24፡15) የሚለውን ኃይለ ቃል ትርጉም እንማማራለን፡፡ እንደሚታወቀው ኢየሩሳሌም ብዙ ጊዜ ጠፍታ በተደጋጋሚ መልሳ የተገነባች ከተማ ናት፡፡  ነገር ግን ይህ የትንቢት ቃል በኢየሩሳሌም የአምልኮው ሥርዐቱና በሌዋውያን ካህናት የሚቀርበው መሥዋዕት ፈጽሞ እንደሚቋረጥ የሚያስረዳ ኃይለ ቃል ነው፡፡ አስቀድሞ በነቢዩ ዳንኤል “የጥፋት ርኩሰት” የተባለውን አንዳንድ ተርጓሚያን  “ሮማውያን በቤተመቅደሱ እሪያ በመሠዋት ጭንቅላቱን ይዘው ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ እንደሚገቡና መቅደሱን እንደሚያረክሱት፤ ይህ በተፈጸመ ጊዜ የኢየሩሳሌም ጥፋት እንደቀረበ አንባቢው ያስተውል ሲል ነው ብለው ይተረጉሙታል፡፡(ፍጻሜው ግን ቅዱስ ጳውሎስ “እኔ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ አዋጅ እየነገረ በእግዚአብሔር ቤተመቅደስ እስኪቀመጥ ድረስ አምላክ ከተባለው ሁሉ ሰዎችም ከሚያመልኩት ሁሉ በላይ ራሱን ከፍ ከፍ የሚያደርገው ተቃዋሚ እርሱ ነው” ብሎ የተናገረለት የሐሳዊው መሲህ መገለጥ ነው፡፡(2ተሰ.1፡4)

 ይህ ሐሳዊ መሲህ ራሳቸውን የአመጻ መሳሪያ ያደረጉትንና ከእውነት ፍቅር ርቀው ሐሰትን የመረጡትን ወገኖች የራሱ ነቢያት(መምህራን) በማድረግ ወደ ምድር ሁሉ ይልካቸዋል፡፡ ብዙዎችም በእነዚህ ሐሳዊያን መምህራን ይስታሉ፤ አንዳንዶች አውቀው ሌሎች ግን ከእውቀት ጉድለት ይስታሉ፡፡ ለዚህ ለሐሳዊ መሲህ ራሳቸውን ነቢያት ብለው የሚጠሩ ወገኖች በትምህርታቸው ክርስቶስ ዓለምን ሊያሳልፍ ያይደለ ነገር ግን ሺህ ዓመታት ሊገዛ ይመጣል ብለው የሚያስተምሩ ሐሳዊያን መምህራን ናቸው፡፡ እንዲህም በማለት ብዙዎችን በትምህርታቸው ያስታሉ፡፡ ይህንንም ሚሌኒየም ብለው ይጠሩታል፡፡
 እንደ እነርሱ አስተምህሮ ክርስቶስ ወደዚህች ዓለም ሦሰት ጊዜ ይመጣል፤ አንደኛው በልደቱ ነው፡፡ ይህ አንዴ ተፈጽሞአል፡፡ ሁለተኛው ዓለምን ሺህ ዓመት ሊገዛ ፤ ሦስተኛው ግን ዓለምን ሊያሳልፍ ይመጣል ይላሉ፡፡ ይህ ግን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለምጽአቱ ካስተማረን ትምህርት ጋር ፈጽሞ የሚቃረን ነው፡፡ እርሱ አንዴ ከቅድስት እናታችን በመወለድ በምድር ተመላልሶ አስተማረ፤ ስለእኛ መዳን በመስቀል ላይ በመዋል መራራ ሞት ተቀበለ፤ በሦሰተኛው ቀንም ሞትን ድል አድርጎ በመነሣት አርባ ቀን ለሐዋርያት ከትንሣኤው በኋላ ታይቶ አስተማራቸው፤ በመጨረሻም ወደ አባቱ እሪና ተመልሶ በአብ ቀኝ ተቀመጠ፡፡ እርሱ እንዳስተማረንም ከእንግደዲህ ዳግም መምጣቱ ዓለምን ለማሳለፍ ነው፡፡ ጌታችን ከዚህ የወጣ ትምህርት   አንዳችም አላስተማረንም፡፡
ስለዚህ እኛ ኦርቶዶክሳዊያን ጌታችን ሁለት ጊዜ ወደ ዓለም ይመጣል፤ አንደኛው የተፈጸመ ሲሆን ሁለተኛው ግን ዓለምን ለማሳለፍ የሚመጣበት  ምጽአቱን ነው ብለን እናምናለን፡፡ በማሃል ግን የሚመጣው ሐሳዊ መሲህ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም የሚያረጋግጥልን ይህንን እውነታ ነው፡፡ ይህ ከጌታችን ዳግም ምጽአት በፊት “እኔ እግዚአብሔር ነኝ ማለትም እኔ ክርስቶስ ነኝ ብሎ የሚመጣው ሐሳዊው መሲህ አለ፡፡ መሲህ ማለት ክርስቶስ ማለት ነውና፡፡ ስለዚህም በክርስቶስ ስም ይምጣል ሲለን ነው፡፡ ይህንንም ቅዱስ ጳውሎስ “እኔ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ አዋጅ እየነገረ በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እስኪቀመጥ ድረስ አምላክ ከተባለ ሁሉ ሰዎችም ከሚያመልኩት ሁሉ በላይ ራሱን ከፍ ከፍ የሚያደርገው ተቋዋሚ እርሱ ነው፡” ብሎ ገልጦታል፡፡ (2ተሰ.1፡4)ስለዚህም እነዚህ ወገኖች እነርሱ የሚሰብኩለት ሺህ ዓመት ምድሪቱን ይገዛል የሚሉለት እውነተኛው የእግዚአብሔር አብ ልጅ የሆነው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሳይሆን ሐሳዊው መሲህ እንደሆነ በዚህ ማረጋገጥ ይቻላል፡፡
እነዚህ ወገኖች ለዚህ ጽንሰ አሳባቸው እንደ መረጃ የሚጠቅሱት ራእይ. 20፡ 1-10 ያለውን ኃይለ ቃል ነው፡፡ በዚህ ኃይለ ቃል ውስጥ አሕዛብን የሚያስተው ዲያብሎስ ሺህ ዓመት እንደሚታሰር፣ ነገር ግን የሐሳዊው መሲህ ጥላ የሆነው ኔሮን ቄሳር እርሱን እንደ አምላክ ያልተቀበሉትን መከራ ክርስቲያኖችን እንደሚያደርስባቸው(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህን ኃይለ ቃል እንዲህ ብሎ ነው የሚፈታው) እርሱን አናመልክም ያሉ ክርስቲያኖችንም ስለ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስክረው ሰማዕትነትን እንደሚቀበሉ እነዚህም ጻድቃን ከክርስቶስ ጋር ሺህ ዓመት እንደሚነገሡ፤ ነገር ግን “ለጥቂት ጊዜ ይፈታ ዘንድ እንደሚገባው” እንደተባለለት (እዚህ ላይ “ለጥቂት ጊዜ” የሚለው ቃል ልብ እንዲባል ያስፈልጋል) የቀድመው እባብ የተባለው በራእይ.12፡9  እንደተገለጠው ዘንዶ የተባለው ሰይጣን እርሱም ሐሳዊ መሲህ ብዙዎችን ያስታል፡፡ ለጥቅት ጊዜ ይፈታል የተባለው በምድረቱ ላይ ሰልጥኖ የሚቆይበት የጊዜ ርዝማኔ ነው፡፡ የጊዜውም ርዝማኔ 42 ወራት ነው፡፡(ራእይ.13፡5) ይህም 3 ዓመት ከስድስት ወር ገደማ ነው፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን ዓለምን ለማሳለፍ ይመጣል፡፡ ሐሳዊው መሲህና ተከታዮችም ወደጥልቁ ገሃነመ እሳት ይጣላሉ፡፡ ክርስቶስን በማመን የጸኑትንና ስለእርሱ የሚቀበሉትን መከራ ታግሠው የቆዩትን ቅዱሳኑን ወደ መንግሥቱ ያፈልሳቸዋል፡፡ ዓለምም ታልፋለች በዚህ መልክ ይጠናቀቃል፡፡  የራእይ 20፡1-10 የያዘው መልእክት ይህ ነው፡፡ 
ክርስቶስ በመስቀሉ ዲያብሎስን ድል ከነሳው በኋላ በእርግጥም ዲያብሎስ ታስሮ ወደ ጥልቁ ተጥሎአል፡፡ ነገር ግን ስንዴውን ከገለባው ይለይ ዘንድ እግዚአብሔር የጥፋት ዝናብን የሚያዘንብበት፣ ጎርፉንም የሚያጎፍበትና ነፋሱን የሚያነፍስበት ጊዜ  ይመጣል፡፡(ማቴ.7፡24-27) በነቢዩ ዳንኤል “የጥፋት ርኩሰት” ተብሎ አስቀድሞ ትንቢት የተነገረለት ሐሳዊው መሲህ እኔ እግዚአብሔር ነኝ እያለ በቤተመቅደስ እስከሚገለጥበት ጊዜ ድረስ ግን ለእርሱ መንገድ ጠራጊዎች የሆኑ ሐሳዊያን ነቢያት ይነሣሉ ብዙዎችንም ያስታሉ፡፡(ማቴ.24፡11፤23-24) ከስብከታቸው አንዱ “ክርስቶስ ዓለምን ሺህ ዓመት ሊገዛ ይመጣል” የሚለው ነው፡፡ በዚህም ብዙዎችን ያስታሉ፡፡ ለሰሚዎቻቸው ስለድንግል ልጅ ስለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚሰብኩ ይመስላሉ፡፡ ነገር ግን ጌታችን ዓለምን ለማሳለፍ ከሚመጣበት ከዳግም ምጽአቱ አስቀድሞ ለዓለም በተግባር ተገልጦ ሕዝቡን የሚያስተው “ለጥቂት ጊዜ ይፈታ ዘንድ አለው” የተባለለት ሐሳዊ መሲህ ነው፡፡ እርሱ በተወሰነለት ጊዜ እኔ ክርስቶስ ነኝ ብሎ ለዓለም ራሱን ይገልጣል፡፡
 በክርስቶስ ባመኑት ላይ ይህ ሐሳዊ መሲህ ምንም ስልጣን የለውም፡፡ ስለዚህም “ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ምስክርና ስለ እግዚአብሔር ቃል ራሶቻቸው የተቆረጡባቸውን ሰዎች ነፍሳት ለአውሬውና ለምስሉም ያልሰገዱትን ምልክቱንም በግንባራቸው በእጆቻቸውም ላይ ያልተቀበሉትን አየሁ ከክርስቶስ ጋር ሺህ ዓመት ነገሡ” ተብሎ ተነገረላቸው፡፡(ራእይ.20፡4) ይህ ማለት ክርስቶስ ኢየሱስ ለዘለዓለም በእነርሱ ላይ ነግሦ ይኖራል ማለት ነው፡፡ ይህ በምን ይረጋገጣል ቢባል “ስለዚህ ነገር ሙታንንም ሕያዋንንም ይገዛ ዘንድ ክርስቶስ ሞቶአልና ሕያውም ሆኖአልና” በሚለው ኃይለ ቃል ማረጋገጥ ይቻላል፡፡(ሮሜ.14፡9) ስለእርሱ ዘለዓለማዊ ገዢነቱ ማወቅ ከተፈለገ ደግሞ “ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊት ዙፋን ይሰጠዋል በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘለዓለም ይነግሣል ለመንግሥቱም ፍጻሜ የለውም” ተብሎ ስለ በመልአኩ የተነገረው ኃይለቃል በቂ ማረጋገጫ ነው፡፡(ሉቃ.1፡32)
 ነገር ግን ሐሳዊ መሲህ በምድር ላይ የሚሰለጥንበት ጊዜ ይመጣል፤ በዚያን ጊዜ በክርስቶስ ያመኑቱ በሐሳዊው መሲህና በእርሱ ጭፍሮች ጽኑ መከራን ይቀበላሉ፡፡ ብዙዎች ደግሞ ስተው ሐሳዊውን መሲህ እንደ ክርስቶስ ተቀብለው ለጥቂት ጊዜአት ይመላለሳሉ፡፡ ዘመኑ ሲፈጸም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው “በአፉ መንፈስ የሚያጠፋው” የተባለለት ክርስቶስ ዓለምን ለማሳለፍ በመለኮታዊው ግርማው ለዓለም ሁሉ ይገለጣል፡፡ ሐሳዊ መሲውንና ግብረአበሮቹን ለዘለዓለም ወደ ጥልቁ ይጥላቸዋል፡፡ ይህ ነው እንግዲህ የራእይ.20፡1-10 ያለው ኃይለ ቃል ትርጉም፡፡) ይቀጥላል…..  

1 comment:

  1. እነዚህ ወገኖች ለዚህ ጽንሰ አሳባቸው እንደመረጃ የሚጠቅሱት ራእይ. 20፡ 1-10 ያለውን ኃይለ ቃል ነው፡፡ በዚህ ኃይለ ቃል ውስጥ አሕዛብን የሚያስተው ዲያብሎስ ሺህ ዓመት እንደሚታሰር፡፡ ነገር የሐሳዊው መሲህ ጥላ የሆነው ኔሮን ቄሳር እርሱን እንደ አምላክ ያልተቀበሉትን መከራ እንደሚያደርስባቸው(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህን ኃይለ ቃል እንዲህ ብሎ ነው የፈታው) እርሱን አናመልክም ያሉ ክርስቲያኖችንም ስለ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስክረው ሰማዕትነትን እንደሚቀበሉ እነዚህም ጻድቃን ከክርስቶስ ጋር ሺህ ዓመት እንደሚነገሡ፤ ነገር ግን “ለጥቂት ጊዜ ይፈታ ዘንድ እንደሚገባው” እንደተባለው (እዚህ ላይ “ለጥቂት ጊዜ” የሚለው ቃል ልብ እንዲባል ያስፈልጋል) የቀድመው እባብ የተባለው በራእይ.12፡9 ላይ ዘንዶ የተባለው ሰይጣን እርሱም ሐሳዊ መሲህ ብዙዎችን ያስታል፡፡ ለጥቅት ጊዜ ይፈታል የተባለው በምድረቱ ላይ ሰልጥኖ የሚቆይበትን የጊዜ ርዝማኔ ነው፡፡ የጊዜውም ርዝማኔ 42 ወራት ነው፡፡(ራእይ.13፡5) ይህም 3 ዓመት ከስድስት ወር ገደማ ነው፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታች ዓለም ለማሳለፍ ይመጣል፡፡ ሐሳዊው መሲህና ተከታዮችም ወደጥልቁ ገሃነመ እሳት ይጣላሉ፡፡ ክርስቶስን በማመን የጸኑትንና ስለእርሱ የሚቀበሉትን መከራ ታግሠው የቆዩትን ቅዱሳኑን ወደ መንግሥቱ ያፈልሳቸዋል፡፡ ዓለምም ታልፋለች በዚህ መልክ ይጠናቀቃል፡፡ የራእይ 20፡1-10 የያዘው መልእክት ይህ ነው፡፡

    ReplyDelete