Sunday, January 6, 2013

ለነፍሳችን ሁለተኛዋ ነፍስ (በቅዱስ ኤፍሬም)



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
28/04/2005
ወዳጄ ሆይ! እምነት ለነፍስህ ሁለተኛዋ ነፍስ እንደሆነች መርምርና እወቅ፡፡ ሥጋ በነፍስ እንድትቆም የነፍስም በሕይወት መኖር በእምነትህ ላይ የተንጠለጠለ ነው፡፡ እምነትህን ብትክድ ወይም ከራስህ ብታርቃት ነፍስህ ምውት ትሆናለች፡፡ በዚህም መሠረት የሚሞት ሥጋችን በነፍስ ላይ ጥገኛ እንደሆነች ነፍሳችንም በእምነት ላይ ጥገኛ ናት፡፡ እምነትም በእግዚአብሔር አብና በመንፈስ ቅዱስ ሕያዋን ባደረገን በእውነተኛ ልጁ ላይ ጥገኛ ናት፡፡
በዚህም እውነት ሰው ነፍሱን በሰማያት ካሉት ጋር ያገናኛታል፡፡ እንዲህ ዓይነት ሰው በነፍሱ በሕይወት ይኖራል፡፡ በሥጋ ሰውነቱም ያያል ይመለከታል፡፡ እንዲሁ እኛም በእምነት በፍቅርና በጥበብ የእግዚአብሔር መልክ ገንዘባችን አድርገን ከመለኮቱ ተካፋይ እንሆናለህ፡፡ ስለዚህም በነፍሳችን የሞትን እንዳንሆን ይህን ድንቅ የሆነ ማሰሪያ እንዳንበጥስ ወይም ነፍሳችን ከእምነት ባዶ እንዳናደርጋት እንጠቀቅ፡፡ ጌታችን ይህን አስመልከቶ እንዲህ ብሎ አስተምሮናልና “ሙታናቸውንም እንዲቀብሩ ሙታንን ተዋቸው”(ማቴ.8፡22)
ይህ አየር በእኛ ላይ በንፍሐት እፍ ሳይባልብን ሥጋችንን በሕይወት የሚያቆያት ነው፡፡ የምንተነፍሰው አየር የተቋረጠበት ሰው ሕይወቱ ትቆማለች፤ በሥጋው የሞተ ይሆናል፡፡ እንዲሁ ራሱን ከእውነተኛ ልጁ ከእግዚአብሔር ቃል የለየ ሰውም በነፍሱ የሞተ ይሆናል፡፡እኔ ሕይወትን የሚሰጠው የእውነተኛ ልጁን ምስክርነት ሳያገኝ ለሞተ ሰው አዝናለሁ፡፡ ልክ እንደ ውቅያኖስ እርሱ የሕይወት ምንጭ ነውና፡፡ 
እርሱ ሰው በመሆን ፈቃዱን እንድናውቀው አደረገን፡፡ ሞትን ድል ለመንሳት ሲል እጅግ መጠማቱ ለእኛ ያለውን ፍቅር አረጋገጠልን፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በእምነት ጻድቅ የሆነ እርሱ በሕይወት እንዲኖር አትሞልናል፡፡ እውነት የተባለው እርሱ ራሱን ዋናው ሥር በማድረግ በጎ ምግባራትን ደግሞ በእርሱ ላይ ባለን እምነት ላይ የተንጠለጠሉ ፍሬዎች አደረጋቸው፡፡ እነሆ መልካም ምግባሮቻችን በእውነትኛው ግንድ በእርሱ ቅርንጫፎች ሆነው በዝተው ፍሬን ይሠጣሉ፡፡እነሆ በሚታይ ምሳሌ የተሰወሩ ምሥጢራት በዓይን እንደሚታዩ ሆነው ተገለጡ፡፡ ሥጋ ልክ ትርፉን ለማግኘት እንደጓጓ ነጋዴ ነው እንዲሁ ሕሊናም ከእርሱ ጋር በእምነትን በሕይወት መርከብ ትርፍን እንደሚሰብስብ መርከበኛ ነው፡፡ 
ሥጋ በነፍስ እንዲቆም ነፍስም ምንም እንኳ ሕያዊት ብትሆን ያለ በጎ ሥራ ሕይወት እንደሌላት፤ ነፍስ በእምነት በሚሠራ የጽድቅ ሥራ በሕይወት እንደምትኖር መጽሐፍ ቅዱስ መስክሮልናል፡፡ በክርስቶስ አምኖ የነበረው አልዓዛር ለዚህ ለምንለው እውነተኛ ምስክር ይሆን ዘንድ ሕያው ሆኖ ተነሣ፡፡ እርሱ ከመቃብር በጠራው በጌታችን ቃል ሕይወቱ ጣፍጣ ሕያው ሆነ፡፡ እንዲሁ በአልዓዛር ምሳሌ አህዛብ በሕቡዕ በሚኖረው ሕይወት ሕያዋን ሆኑ፡፡ በተቃራኒው ደግሞ በአይሁድ ሥራ ምሳሌ ወንበዴው ራሱን ሰቀለ እንደ ውርስ አድርጎ ሞቱን ለጸሐፍት ፈሪሳዊያን ተወላቸው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በእርሱ ላይ ባለን እምነት በመንፈስ ቅዱስ ሕያዋን ሆነን እምነታችንን ጠብቀን እንድንኖር ይርዳን፤  በክርስቶስ ለምወዳችሁ አባቶቼና እናቶቼ ወንድሞቼና እኅቶቼ ሁሉ መልካም የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት ይሁንላችሁ፡፡     


No comments:

Post a Comment