Friday, January 20, 2012

የጽሙና ሕይወት ወዳዱ ዮሐንስ ሶርያዊ ስለ ጥምቀት ያስተማረው ትምህርት


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
11/05/2004


ሥጋዊው ማኅፀን የሚታይ ሥጋን ለብሰን እንድንወለድ በማድረግ ከዚህ ዓለም ፍጥረታት ቁጥር እንዲደምረንና የዚህን ዓለም ውበት ለማድነቅ እንደሚያበቃን እንዲሁ ጥምቀትም መንፈሳዊ ልደትን እንድንወለድበት የተዘጋጀ ማኅፀን ነውና ከሰማያውያን ፍጥረታት ጋር እንድንደመርና መንፈሳዊውን ዓለም ለማየትና ለማድነቅ እንድንበቃ ያደርገናል ፡፡ በሥጋ ካልተወለድን በቀር ግሩም የሆነውን የዚህን ዓለም ውበት ማየት እንደማንችል ሁሉ በጥምቀት ካልሆነ በቀር እውነተኛውን ዓለም ለማየት አንበቃም ፡፡ ጌታችን ለኒቆዲሞስ እንደተናገረው አንድ ሰው አስቀድሞ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልምና ፡፡…(ዮሐ.፫፥፫)
ያልተጠመቀ ሰው በኃጢአት ምክንያት ልክ እንደሞተ ሰው የአካል መገጣጠሚያዎቹ የተለያዩ የሚከረፋና የሚሸት ሬሳ ነው ፡፡ ሥጋ በነፍስ ምክንያት ሕያው እንደምትሆን ነገር ግን ነፍስ ብትለያት ፈርሳና በስብሳ ወደ አፈርነቱዋ እንድትመለስ በክርስቶስ አምኖ ያለተጠመቀም ሰው እጣ ፈንታው ይህ ነው፡፡ በክርስቶስ የማዳን ሥራ በጥምቀት ይህ ሰው ክርስቶስን ቢለብሰው የእግዘአብሔር አርዓያንና አምሳልን ገንዘቡ ከማድረጉ በተጨማሪ  በነፍስ ምትክ መንፈስ ቅዱስ ነፍሱ ይሆንለታል፡፡ ስለዚህም በእግዚአብሔር ዘንድ ሕያ እንጂ ሙ አይባልም፡፡
 ቅዱስ ጳውሎስ “… እኛም በአዲስ ሕይወት እንመላለስ ዘንድ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን ፡፡”(ሮሜ.፮፥፬) እንዲሁም “ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችሁታል”(ገላ.፫፥፳፯) እንዲል ከእግዚአብሔር ጋር የነበረው ጠላትነት ጠፍቶ ከእርሱ ጋር ማኅበርተኞች ሆነናል፡፡  በክርስቶስም ሰውነት በኩል የመለኮቱ ተካፋዮች ሆነናል፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ጳውሎስ ይህ እንደሆን ለማስረዳት “አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም ፤ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም ፤ወንድም ሴትም የለም ፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና”አለን ፡፡ ( ገላ.፫፥፳፰) ጥምቀትን ለእኛ በሞትህ በመመሥረት  ሕያዋን ያደረገኸን አምላካችን ሆይ ላንተ ክብር ይሁን!!!

No comments:

Post a Comment