Saturday, July 7, 2012

የቤተ ክርስቲያንን ለቤተ ክርስቲያን የገዳምን ለገዳማውያን



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
29/10/2004
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱስ ጴጥሮስ …ትወደኛለህን? ብሎ ከጠየቀውና እርሱም አዎን ብሎ ከመለሰ በኋላ “... ግልገሎቼን አሰማራ…ጠቦቶቼን ጠብቅ … በጎቼን አሰማራ” ብሎ መንጋውን እንዲጠብቅ አደራ እንደሰጠው እናውቃልን፡፡(ዮሐ.19፡15-17)ይህ ሓላፊነት ምንም እንኳ ለእርሱ ይነገረው እንጂ ለሐዋርያት ሁሉ የተሰጠ ሓላፊነት ነበር፡፡ እነርሱም የክርስቶስን መንጋ ከሥጋና ከመንፈስ ርሃብ ጠብቀው የድርሻቸውን ተወጥተው አልፈዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ማለት ሕጻናት፣ ወጣቶችና አረጋዊያን በአንድነት የሚኖሩባት፣ በምድር ያለች ግን ሰማያዊት፤ ቅዱሳን መላእክት፣ ቅዱሳን ነፍሳትና በምድር ያለነው በጥምቀት ከክርስቶስ ጋር በሞቱ ለዚህ ዓለም ኃጢአት የሞትን፤ መንፈስ ቅዱስ በሚሰጠን ሕይወት ሕያዋን የሆንንና በትንሣኤ ሕይወት የምንመላለስ የምንኖርባት፤ ጌታችን መድኀኒታችን የሚገዛትና የሚመራት ከምድር እስከ ሰማይ የተተከለች ዘለዓለማዊት መንግሥት ናት፡፡ ገዳም ግን መነኩሳት በፈቃድ የብሕትውናን ሕይወት መርጠው የሚኖሩባትና ለእነርሱ ብቻ የምትስማማ ሆና ሥርዐት የተበጀላት መንፈሳዊት ሥፍራ ናት፡፡


ስለዚህም ምንም እንኳ አንዳንድ ነገሮቻቸው የሚመሳሰሉ ቢሆኑም ሙሉ ለሙሉ የገዳማዊውን ሥርዐት ለቤተ ክርስቲያን የቤተክርስቲያንን ሥርዐት ለገዳማዊያን ተግብሮ መጠቀመም ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን በሥሩዋ ያሉትን ሕጻናት፣ ወጣቶች፣ እንዲሁም አረጋውያን በሥጋም በነፍስም በድህነት ምክንያትና በእውቀት ማነስ በኃጢአት ተሰነካክለው እንዳይወድቁ ለመታደግ ክርስቲያናዊ ሰብእናን እንዲላበሱ ስትል ለማስተማር የምትተጋና የበጎ አድራጎት ሥራዎችን አብዝታና አስፍታ ልትሠራ የሚገባት መንፈሳዊት ተቋም ናት እንጂ እንደ ገዳማውያን በጸሎትና በጦም ብቻ  ጽሙድ ሆና የምትኖር ተቋም አይደለችም፡፡
ገዳም ለራሳቸው ምን ማድረግ እንደሚገባቸው የሚያውቁ ወገኖች የሚኖሩባት ሥፍራ ስትሆን ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንመጣ ግን ቀኝና ግራቸውን ያለዩና ክትትል የሚያስፈልጋቸው ሕጻናትና አብነት የሚፈልጉ ዓለማችንን ራስ ሆነው መምራት የሚገባቸው ወጣቶች የሚኖሩባት እንዲሁም እርዳታና ድጋፍ የሚያስፈልጋቸው አረጋውያን በውስጡዋ አቅፋ የያዘች መንፈሳዊት ተቋም ነች፡፡ ስለዚህም እነዚህን ባገናዘበ መልኩ ልትንቀሳቀስ እንጂ ለአዋቂዎች ብቻ በሚመች ሥርዐት ልትመላለስ አይገባትም፡፡ 
በሐዋርያት ዘመን የነበረችው ቤተ ክርስቲያን በመካከሉዋ አንድም የሥጋም ሆነ የመንፈስ ደሃ አልነበረባትም፡፡(የሐዋ.4፡34) ይልቁኑ ለተቸገሩት የምትደርስ ነበረች እንጂ፡፡(1ቆሮ.16፡1-3) ይህ የሚያሳየን ሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን ልትሠራቸው የሚገቧትን ሥራዎች እንድትሠራ በማድረግ ሓላፊነታቸውን በአግባቡ መወጣታቸውን ነው፡፡ 
አሁን ግን ቤተ ክርስቲያናችን ሓላፊነቱዋን ዘንግታለች፤ ደሃውን ረስታለች፣ ክርስቶስን መስሎ ራስና መሪ ሊሆን የሚገባው ወጣት ለዚህ ማዕረግ እንዲደርስ ምንም ዓይነት ድጋፍ አላደረገችለትም፡፡ ይልቁኑ በኃጢአት ጭቃ ውስጥ ተዘፍቆ በሥጋም በመንፈስም ደህይቶና ጎስቁሎ እንዲኖር ረስታዋለች፤ ሴቶቻችንም ተጠቅተውብናል፣ ሕፃናት ከሥርዐት ወጥተው አንደበታቸው ለስድብ ተከፍቶአል፡፡ እነዚህ ሁሉ ቤተ ክርስቲያን የሥራ ድርሻዋን ዘንግታ ገደማዊ ሥርዐትን በመከተል ሕጻናትን፣ ወጣቶችን፤ ድሆችን እንዲሁም ሴቶችን በመርሳቱዋ ምክንያት የመጡባት ችግሮች ናቸው፡፡ ይህ ያልተስተዋለ ችግር እኛን መንጎቹዋን ለሥጋም ለመንፈስም ድህነት አጋልጦ ሰጥቶናልና በውጪም በውስጥም ሰቆቃችን በዝቶአል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ልጆቹዋን ልክ እንደ ሰጎን ረስታለች የእርሱዋ እንዳልሆኑ በልጆቹዋ ጨክናለች(ኢዮ.39፡13-16)!!!!!!!!!!!!   ዋይ ዋይ ዋይ ........ 

1 comment:

  1. በርግጥ ይህን ህብረተስቡ በቀላሉ ለመቀበል ይከብዳዋል ምክንያቱም ቤተክርስትያን ህዝቡ የሚያቃት ስትቀበል እንጂ ስትሰጥ አይደልም አንጡ እንጂ እንኩ የሚል ትምህርት አይሰማም ለምን ብሎ እንኳን ቢጠይቅ በእግዚአብሔር ላይ እደተቃወመና እዳጉረመረመ እደተመርረ ትደርጎ ስሚቆጠር እይጠይቅም ግን ትክክለኛው የቤ/ክ ትምህረታ መግቦታ በስጋም በነፍስም ነው። ይህንም ጌታችን መድሀንታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ እራሱ በስጋዌው ዘመን ህዝቡን በመንፈስም በስጋም ሲመግባቸው ነበር። ሐዋርያቱም ፈለጉን ተከትለው አርገውት አልፈዋል በዘመናችን የተዘነጋና እንደነውርም እየታየ እስኪመስል ድረስ ተዘንግታል በሎሎች እህት ቤ/ክ ግን እሰካሁንም አለ ድሆችንና ህጻናት አረሱም። እኛ ጋን እዳይተገበር ያረጉት እነሆድ አምላኩና እናአይጠጌ አይኔኬ ናቸው ጥቅማቸው እዳይቀር ከምቾታቸው እንዳይጓደል ድሀውን ረስተውታል። ህዝቡ ውጫወው አፉ በይጠይቅ ውስጣዊው አፉ መጠየቁ አይቀርም ግን አውጥቶ አይነግረውም እንኳንስ ለሰው ራሱም አይነግረ የተሳሳተ አርጎ ስለሚያስብ ይሸሸዋል ።

    ReplyDelete