Friday, December 21, 2012

አርምሞ (ለአንድ ወንድሜ የጻፈኩት)



ከዲ/ን ሽመልስ መርጊ
12/04/2005
አርምሞ ከራስ ጋር ለመሆን ጊዜን ከመስጠት የሚጀምር ነው፡፡ እንዲያው በባዶ ግን አይደለም፤ አስቀድሞ የግል ጊዜ ሊኖረን  ግድ ነው፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም ዐይን ውስጥ ትንሽ ብናኝ ብትገባ እንደምትረበሽና እንደምትታወክ ከዚያም በላይ አንደምታለቅስ እንዲሁ ሕሊናም ጥቃቅን በምንላቸው ኃጢአቶች መረበሹና መታወኩ አይቀሬ ነው፡፡ ስለዚህ ሕሊናችን በኃጢአት ከተያዘ መረጋጋትን ገንዘባችን ማድረግ አይቻለንም፡፡
ነገር ግን ሕሊናችን ከኃጢአት ነጽቶ እርጋታን ገንዘቡ ሲያደርግ በጥሙና ሆነን ያለ አንዳች መደነቃቀፍ መንፈሳዊውን ዓለምና ምሥጢር ወደ መረዳት እንመጣለን፡፡ ስለዚህ ወደ ጥሙና ሕይወት ከመግባታችን በፊት አስቀድመን ለንስሐ ራሳችንን ማዘጋጀት አለብን በኋላም ንስሐ መግባት፡፡ በንስሐ የእግዚአብሔር ፍቅር በውስጣችን ይቀጣጠላል፡፡ በዚህም ምክንያት ስለእግዚአብሔር በጥልቀት ለማወቅ እጅግ እንጓጓለን፡፡ በዚህ ሰዓት ነው እንግዲህ የምናነባቸውን ምንባባትና የምንጸልያቸውን ጸሎታት መምረጥ ያለብን፡፡ ያለበለዚያ ፈጽሞ አርምሞን ገንዘባችን ማድረግ አይቻለንም፡፡ ስለዚህ ሌላውን የሚነቅፉና ለጠላት ጥፋትን የሚለምኑ ምንባባትንና ጸሎታትን ከማንበብ መከልከል ተገቢ ነው፡፡

እነዚህ እይታችንን ወደ እግዚአብሔር ሳይሆን ወደ ሰዎች ስለሚያደርጉብን ከሰማያዊ ተመስጦ ያወጡናል፡፡ ስለዚህ በዚህ ጊዜ ራስን በሥነ ምግባር የሚያንጹ ፍቅረ እግዚአብሔርንና ፍቅረ ቢጽን የሚሰብኩ መጻሕፍትንና ከእግዚአብሔር ጋር ሊያነጋግሩ የሚችሉ (ምክንያቱም እርሱ የፍቅር አምላክ ነውና) ጸሎታትን መርጦ መጸለይ ይገባል፡፡ እንዲህ በማድረግህ ብቻ ግን የጽሙና ሕይወትን ለማግኘት ትችላለህ አይባልም፡፡ የጽሙና ሕይወት ልምምድን ይፈልጋል፡፡ ስለዚህ ለልምምድ እንዲረዳህ ከመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ወይም ካነበበከው የመጽሐፍ ክፍል የተረዳኸውን የምታሰፍርበት ማስታወሻ ደብተር ልታዘጋጅ ይገባሃል፡፡ በዚያ ላይ የተረዳኸውንና ያልገባህን እንዲሁም ወደ አምላክህ የምታደረሰውን ጸሎት አስፍርበት፡፡
ሁሌም ይህን ለማድረግ ትጋ፤ በዚህ ሰዓት ሕሊናህ አንድን ነገር በጥልቀት መመርመርን ይለማመዳል፤ ሰዓት ሳይመርጥ መጸለይንም ገንዘቡ ያደርጋል፡፡ ይህም ቀስ በቀስ ወደ አርምሞ ሕይወት ይመራሃል፡፡ የአርምሞን ሕይወት በነዚህ ከላይ በገለጥኳቸው መንገዶች ገንዘብህ ካደረግህ ከሰው ጋርም ሆንክ ብቻህን አንተን ከተመስጦ ሕይወት የሚያወጣ የለም፡፡ አንደበትህ ሳይከፈት በሕሊና አምላክህን ታመሰግናለህ ትለማመናለህ ይህ በመንፈስ መጸለይ ይባላል፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም እንዳለው፡- ዐይንህ ከምንባብ ሲያርፍ አእምሮ በተመስጦ ወደ ሰማየ ሰማያት በመነጠቅ የእግዚአብሔርን እውቀት በጥልቀት ይመረምራል፡፡ እእምሮህ ከተመስጦ ሲመለስ ዐይንህ ደግሞ ወደ ምንባብ ይመለሳል፡፡ በዚህ መልክ ስትበላም ስትጠጣም ስትሠራም ስታርፍም ስትተኛም ስትነቃም ሁሌም በተመስጦ ሕይወት ውስጥ መሆን ይቻልሃል፡፡ ይህም አርምሞን ገንዘብህ እንድታደርግ ይረዳሃል፡፡
 ከመጠጥ ራቅ መጠጥና ኃጢአት አንድ ናቸው ብኩን ያደርጉሃል፡፡ ከሰው ይልቅ መጻሕፍት ወዳጆችህ ይሁኑ፡፡ የመጻሕፍት ወዳጅ ከሆንክ ዐይኖችህ ጤናሞች ስለሚሆኑ መልካም ባልንጀራህ ማን እንደሆነ ትለያለህ፡፡ ስለዚህ አንተ በሰው አትሰናከልም ሰውም ባንተ አይሰናከልም፡፡ ሕሊናህም እነርሱን በመበደልህ ምክንያት አይረበሽም፡፡ 
በተቻለ መጠን ከሚወድህ አምላክህ ጋር ያለህ ሕይወት የተገለጠ እንዳይሆን ተጠንቀቅ፡፡ ከትዕቢትም በሚከፋው ከንቱ ውዳሴ ተይዘህ እንዳትወድቅ፡፡ አይሁድ ክርስቶስን አውቀውት ነበር ነገር ግን በከንቱ ውዳሴ እግር ብረት ታስረው ነበርና እያወቁ ክርስቶስን ሰቀሉት ደሙ በእኛና በልጆቻችን ላይ ይሁን አሉ፡፡ 
ወዮ ከከንቱ ውዳሴ በላይ ምን የከበደ ወጥመድ አለ? ስለዚህ ወንድሜ ከከንቱ ውዳሴ አጥብቀህ ሽሽ፡፡ ለእኔም ለኃጥኡ ወንድምህ ጸልይልኝ፡፡ አዳማዊ የሆነውን ብዙ መልካም ሥራዎችን የምንሠራበትን ነገር ግን ጥቂት የምንናገርበትን የአርምሞ ሕይወትን ይሰጠን ዘንድ የሚወደን አባታችን እግዚአብሔር አብ፣ ፍቅሩን በቃል ሳይሆን በተግባር የገለጠልን እግዚአብሔር ወልድ፣ ሰውነታችንን መቅደሱ አድርጎ መልካም ሥራን እንድንሠራና ምን ብለን መጸለይ እንደሚገባን በውስጣችን ሆኖ አባት ልጁን እንደሚያስተምር በፍቅር የሚያስተምረን፣ እውነትን ወደ ማወቅ የሚመራን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ይርዳን ለዘለዓለሙ አሜን!!! 

4 comments:

  1. ከሰው ይልቅ መጻሕፍት ወዳጆችህ ይሁኑ፡፡ የመጻሕፍት ወዳጅ ከሆንክ ዐይኖችህ ጤናሞች ስለሚሆኑ መልካም ባልንጀራህ ማን እንደሆነ ትለያለህ፡፡ Kale hiwotn yasemaln tsegawn yabzalh be edmi betina ytebkln endante aynetu memhrann yabzaln !!!

    ReplyDelete
  2. ቅዱስ ኤፍሬም እንዳለው፡- ዐይንህ ከምንባብ ሲያርፍ አእምሮ በተመስጦ ወደ ሰማየ ሰማያት በመነጠቅ የእግዚአብሔርን እውቀት በጥልቀት ይመረምራል፡፡ እእምሮህ ከተመስጦ ሲመለስ ዐይንህ ደግሞ ወደ ምንባብ ይመለሳል፡፡ በዚህ መልክ ስትበላም ስትጠጣም ስትሠራም ስታርፍም ስትተኛም ስትነቃም ሁሌም በተመስጦ ሕይወት ውስጥ መሆን ይቻልሃል፡፡ ይህም አርምሞን ገንዘብህ እንድታደርግ ይረዳሃል፡
    MEMIHIR KALE HIYIWET YASEMALIN YIHIN YEABOTACHACHIN YETSELOT HIYIWET EGNAM GENIZEB EDINAREGEW MEDIHIN ALEM KIRISITOS YIRIDAN

    ReplyDelete
  3. ቅዱስ ኤፍሬም እንዳለው፡- ዐይንህ ከምንባብ ሲያርፍ አእምሮ በተመስጦ ወደ ሰማየ ሰማያት በመነጠቅ የእግዚአብሔርን እውቀት በጥልቀት ይመረምራል፡፡ እእምሮህ ከተመስጦ ሲመለስ ዐይንህ ደግሞ ወደ ምንባብ ይመለሳል፡፡ በዚህ መልክ ስትበላም ስትጠጣም ስትሠራም ስታርፍም ስትተኛም ስትነቃም ሁሌም በተመስጦ ሕይወት ውስጥ መሆን ይቻልሃል፡፡ ይህም አርምሞን ገንዘብህ እንድታደርግ ይረዳሃል፡፡ KALE HIOWETEN YASEMALEN EGIZABEHER AMELAK TSEGAAWN YABZALEH REGEME EDME ENA TENAWN YISTILEN !!!

    ReplyDelete
  4. ከሰው ይልቅ መጻሕፍት ወዳጆችህ ይሁኑ፡፡ የመጻሕፍት ወዳጅ ከሆንክ ዐይኖችህ ጤናሞች ስለሚሆኑ መልካም ባልንጀራህ ማን እንደሆነ ትለያለህ፡፡ ስለዚህ አንተ በሰው አትሰናከልም ሰውም ባንተ አይሰናከልም፡፡ ሕሊናህም እነርሱን በመበደልህ ምክንያት አይረበሽም፡፡

    ReplyDelete