Friday, February 24, 2012

ሠዓሊት በተፈጥሮ


ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
16/06/2004

እግዚአብሔር አምላክ ሴትን ልጅ ጥበብን የምትወድ ሠዓሊት አድርጎ ፈጠራት፡፡ ስለዚህም ውስጣዊውንና ውጫዊውን የሰውነት ክፍሎቹዋን እንደ ሸራ በመጠቀም ልታስተላለፍ የምትፈልገውን መልእክት በሰውነቱዋ ሸራ ላይ ትሥልልናለች፡፡ እኛም ወንዶች ደግሞ አድናቂዎቿና ተማሪዎቿ ነን፡፡ ባለን እውቀት ላይ ተጨማሪ እውቀቶችን ከእርሱዋ እንጨምራለን፡፡ እንዲህም ስለሆነ እነርሱ ሁል ጊዜ በሕሊናቸው የሚመላለሰውን በጎም ይሁን ክፉ አሳብ በሰውነታቸው ሸራ ላይ ለመሣል ሲተጉ እኛ ወንዶች ደግሞ ሥዕላቸውን አይተን ለማድነቅና ለመማር እንተጋለን፡፡ እነርሱ ልክ እንደ ሠዓሊ በዝምታ መልእክታቸውን በሰውነታቸው ሸራ ላይ ሲያስተላለፉ፤ እኛ ደግሞ በዝምታ የጥበብ ጥማችንን ስናረካና ከመልእክቶቻቸው ስንማር እንገኛለን፡፡
ይህን ግን ምናልባትም ዘመኑ የተረዳው አይመስለኝም፡፡ ሴትን ልጅ አታጊጪ ብሎ መከልከል አንድ ሠዓሊን አትሣል ብሎ እንደ መከልከል ይቆጠራል፡፡ ሠዓሊን አትሣል ብለን ብሩሹንና ሸራውን ልንቀማው እንችላለን፡፡ ሴትን ልጅ ግን አትሣዪ ብሎ በምን ማቆም እንዴት መከልከል ይቻላል? እርሱዋ ሥዕሉዋን መሣል የምታቆመው ይህችን ዓለም በሞት የተሰናበተቻት እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ለእርሱዋ ብሩሹዋ ማስተዋሉዋ ነው፤ ቀለሞቹዋም በነፍሱዋ ውስጥ ናቸው ሸራዎቹዋም ነፍስና ሥጋዋ ናቸው፡፡ በማስተዋል ብሩሽ፣ በነፍሱዋ ውስጥ ባሉ ቀለማት ነፍሱዋንና ሥጋዋን በውበት ታስጌጣቸዋለች፡፡

Wednesday, February 22, 2012

ኑ ቀረብ በሉ!


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
15/04/2004
ፍቅር የሆነ አምላካችን ምን ያህል እኛን እንዳከበረን እስቲ ለአንድ አፍታ ቆም ብልን እናስበው፡፡ አፍቃሪያችን አስቀድሞ በራሱ አርአያና አምሳል ፈጠረን ስለዚህም ክብራችን በመላእክት ዘንድ እጅግ ታላቅ ሆነ፡፡ የእግዚአብሔር መልክ አለንና እጅግ አከበሩን፡፡ ስለዚህም እርሱን እንዳገለገሉት ቆጥረው ቅዱሳን መላእክት እኛን አገለገሉን፡፡ ይህን አስመልክቶ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ አለን “እግዚአብሔር አምላክን በላይ በሰማይ የሚያገለግሉት ቅዱሳን መላእክት እኛን አገለገሉን፡፡ ይህ እግዚአብሔር አምላክ እኛን ምን ያህል እንዳከበረን የሚያሳየን ነው፡፡” ይህ በእርግጥ ድንቅ ነው፡፡
አክብሮ የፈጠረውን ሰብእናችንን በኃጢአት በማዋረዳችን ምክንያት ፈጣሪያችን ተመርሮብን ለዘለዓለም ቆርጦ አልጣለንም፡፡ ነገር ግን ፍቅሩ አገብሮት እኛን እጅግ ሊያከብረንና ሰይጣን ከማይደርስበት ከፍታ ከፍ ከፍ ሊያደርገን ሰማይና ምድርን የፈጠረ አምላክ ከድንግል ቅድስት እናታችን ማኅፀን ተወሰነ፡፡ ሥጋና ነፍስን ከእርሱዋ በመንሳትም ተወለደ፡፡ በዚህም ባሕርያችንን አምላክ አደረገው፡፡ ቅድስት እናታችንንም ሰማይ አደረጋት፡፡ አሁን እኛ ክርስቲያኖች “አባታችን ሆይ በሰማይ የምትኖር” ስንል እነሆ እርሱዋን ሰማይ አድርገን ነው፡፡ ምክንያቱም ወልድ ባለበት አብም መንፈስ ቅዱስም አሉና፡፡ እንዲህ አድርገህ እጅግ ያከበርከንና ያፈቀርከን ፈጣሪያችን ሆይ ላንተ ምን አንደበት ነው ምስጋናን ማቅረብ የሚቻለው? 
እርሱ በዚህ ድንቅ ቸርነቱ ብቻ አላበቃም እኛንም እንደ እናቱ ለራሱ ማደሪያ በማድረግ ሰማይ አደርጎናልና እናመሰግነዋለን፡፡ እርሱ በቃሉ“ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ እርሱ በእኔ ይኖራል እኔም በእርሱ እኖራለሁ" ”(ዮሐ.6፡56)አለን፡፡ ስለዚህም ሥጋውን ስንበላ ደሙንም ስንጠጣ ከድንግል ማኅፀን ተፀንሶ የነበረው ጌታ በእኛም ሰውነት ውስጥ ያድራል፡፡ በመሆኑም እኛም እንደ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በአማን ሰማዩ ሆንን፡፡ ድንግል ሆይ ራስሽን ለፈጣሪያችን ሰማይ በማድረግ እኛም ለእርሱ ሰማይ እንድንሆን ስላበቃሽን እናመሰግንሻለን፡፡ አሁን “አባታችን ሆይ በሰማይ የምትኖር” ስንል የእኛን ሰውነት ሰማይ አድገህ የምትኖር አክባሪያችን ሆይ ስምህ ይቀደስ እያልነው ነው፡፡ ለዚህ ድንቅ ቸርነትህ ምን ዐይነት ምስጋናን ማቅረብ ይቻለን ይሆን?

Sunday, February 19, 2012

ያልታወቀው የጦም ጥቅም



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
12/06/2004



ብዙዎቻችን የጦም ጥቅሙ ከምግብ ተከልክለን ራሳችንን ከእግዚአብሔር ፊት በማዋረድ ከእርሱ ዘንድ ሰማያዊ ጸጋን ማግኘታችን ነው፤ ብለን እናስባለን፡፡ ይህ ፍጹም ትክክል ነው፤ ነገር ግን ክብር ለእርሱ ይሁንና ሌላ እኛ የማናውቀው በጦም የኖሩ ቅዱሳን የሚያውቁት አንድ ልዩና ግሩም የሆነ ጥቅም አለው፡፡ እንዲህ ሲባል “ከእኛ ምን ተሰውሮ! በጦም ነፍሳችን ለሥጋ ከመትጋት ወጥታ ከእግዚአብሔር ጋር በተመስጦ በመኖሯ ነፍሳችንም ሥጋችም የሚጠቀሙት ጥቅም አላቸው፡፡” ብላችሁ ትመልሱልኝ ይሆናል፡፡ እንዲህ የመለሳችሁ እንደሆነ እኔ ልገልጠው ያሰብኩትን ጭብጥ አላገኛችሁትምና ሌላ ሞክሩ፡፡ ወይም "ከጤና አኳያ ሰውነታችንን ከምግብ በከለከልናት ጊዜ አካላችን በራሱ የአሠራር ሥርዐት በሰውነት የተከማቸውን ስብ ወደ መጠቀም ስለሚመጣ የስብ ክምችታችን ይቀነሳል፤ ስለዚህም በስብ ክምችት ምክንያት ከሚመጡ ሪህ፤ ደም ግፊትና ስኳር እንዲሁም እነዚህን ከመሰሉ ሕመሞች ይጠብቀናል፡፡ ስለዚህም ሰውነታችንን ጤናማ በማድረግ ያለምንም የጤና መጓደል መንፈሳዊ የሆኑ ተግባራትን ለማከናወን ስለሚያገለግለን ነው” ብላችሁ ልትመልሱ ትችላላችሁ፡፡ እኔ ግን መልሱን አላገኛችሁትም ነው መልሴ፡፡ “እሺ ይህ ካልሆነ እኛ ጌታችንን መስለን በመጦም ሰይጣንን ድል መንሳታችን ነው ጥቅሙ” ትሉኝ ይሆናል፡፡ እርሱም ጥሩ መልስ ነው፡፡ ምክንያቱም ጦም ነፍስን እንደ መልአክ ስለሚያደርጋት ወይም የሥጋ ሥራ ስለሚቀልላት ዐይኖቹዋ በጦም ሰዓት አጥርተው ይመለከታሉና በቀላሉ ሰይጣን ድል ሊነሳት አይቻለውምና ነው፡፡ ነገር ግን ከላይ የመለሳችኋቸው ሁሉ ትክክለኛ መልሶች ቢሆኑም እኔ ልል የፈለግሁትን ግን አላገኛችሁትም፡፡ "እሺ ከእነዚህ ውጪ ምን ልዩ የሆነ መልስ ሊኖር ይችላል? ብላችሁ ጽምፃችሁን አሰምታችሁ ልትናገሩኝና የእኔንም መልስ ጆሮአችሁን አቀቅራችሁ ልትጠባበቁኝ ትችላላችሁ፡፡