ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ
14/09/2004
ቅዱስ ጳውሎስ
ለቆላስይስ ሰዎች በላከው መልእክቱ ም.፬፥፲፪ ላይ ያለውን ኃይለ ቃል ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በተረጎመበት ፲፪ኛው ድርሳኑ በዘመኑ የሚፈጸመውን የሰርግ ሥርዐት መሠረት በማድረግ ሰርግን አስመልክቶ ሰፋ ያለ ትምህርትን
ሰጥቶአል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በሰርግ ምክንያት የሚወጡትን ወጪዎችንና ሁካታዎችን አጥብቆ የሚቃወም አባት ነው ፡፡ በዚህም
ጽሑፍ ይህን ወደማስተዋል ልንመጣም እንችላልን ፡፡
"...ትዳር ምንድን ነው? ትዕይንት(ትያትር)
ነውን? አይደለም፡፡ ምንም እንኳ እናንተ ለትዳርና ለምሳሌው አክብሮት
ባይኖራችሁ እንኳ ትዳር ግሩም ምሥጢርና የታላቅ መንፈሳዊ ምሥጢር ምሳሌ ነው ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህ ሲያስተምር “ይህ ምሥጢር ታላቅ
ነው” ይልና ጨምሮ “እኔ ግን ስለ ክርስቶስና ስለቤተክርስቲያን እላለሁ” ይላል፡፡(ኤፌ.፭፥፴፪) ጋብቻ የቤተክርስቲያንና የክርስቶስ
ምሳሌ ነው ፤ እንዲህ በከበረ ምሥጢር ላይ ዳንኪረኞችን በመጋበዝ ዝሙትን ታስተዋውቃላችሁን ? ነገር ግን ከእናንተ መካከል አንዱ
እኔን፡- እንዲህ ስትል ደናግላን ወይም ያገቡት አይጨፍሩ እያልክ ነውን ? እንግዲያስ እነርሱ በዚህ ሠርግ ላይ ካልጨፈሩ ማን ሊጨፍር
ነው ? ብሎ ሊጠይቅ ይችላል ፡፡ የእኔ መልስ ማንም አይጨፍር የሚል ነው ፡፡

