Tuesday, May 22, 2012

ሠርግ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እይታ



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ 
14/09/2004
ቅዱስ ጳውሎስ ለቆላስይስ ሰዎች በላከው መልእክቱ ም.፬፥፲፪ ላይ ያለውን ኃይለ ቃል  ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በተረጎመበት ፲፪ኛው ድርሳኑ በዘመኑ የሚፈጸመውን የሰርግ ሥርዐት መሠረት በማድረግ ሰርግን አስመልክቶ ሰፋ ያለ ትምህርትን ሰጥቶአል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በሰርግ ምክንያት የሚወጡትን ወጪዎችንና ሁካታዎችን አጥብቆ የሚቃወም አባት ነው ፡፡ በዚህም ጽሑፍ ይህን ወደማስተዋል ልንመጣም እንችላልን ፡፡    
"...ትዳር ምንድን ነው? ትዕይንት(ትያትር) ነውን? አይደለም፡፡  ምንም እንኳ እናንተ ለትዳርና ለምሳሌው አክብሮት ባይኖራችሁ እንኳ ትዳር ግሩም ምሥጢርና የታላቅ መንፈሳዊ ምሥጢር ምሳሌ ነው ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህ ሲያስተምር “ይህ ምሥጢር ታላቅ ነው” ይልና ጨምሮ “እኔ ግን ስለ ክርስቶስና ስለቤተክርስቲያን እላለሁ” ይላል፡፡(ኤፌ.፭፥፴፪) ጋብቻ የቤተክርስቲያንና የክርስቶስ ምሳሌ ነው ፤ እንዲህ በከበረ ምሥጢር ላይ ዳንኪረኞችን በመጋበዝ ዝሙትን ታስተዋውቃላችሁን ? ነገር ግን ከእናንተ መካከል አንዱ እኔን፡- እንዲህ ስትል ደናግላን ወይም ያገቡት አይጨፍሩ እያልክ ነውን ? እንግዲያስ እነርሱ በዚህ ሠርግ ላይ ካልጨፈሩ ማን ሊጨፍር ነው ? ብሎ ሊጠይቅ ይችላል ፡፡ የእኔ መልስ ማንም አይጨፍር የሚል ነው ፡፡

Monday, May 21, 2012

“መስቀል ለእኔ”



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
14/09/2004
መስቀል ስል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበትን ያን መስቀል ማለቴ ነው፡፡ እንዲያም ሲሆን ደግሞ እንደመንፈሳዊ ትርጉሙ እንጂ  እንደ ሥጋዊያን አይደለም አረዳዴ፡፡ እነርሱ በመስቀሉ ክርስቶስን አይመለከቱትም፤ በክርስቶስ ደግሞ የመስቀሉን መንፈሳዊ ትርጉም አይረዱት ቁሳውያን ናቸው ፡፡ እግዚአብሔር የእውቀቱን ደጅ ይክፈትላቸው፡፡ ታመዋል ወይም እነዚህ ወገኖች ጣዖት አምላኪያን ሆነዋል፡፡ ሰዎችን እንዲህ እንዲስቱ  የሚያደርጋቸው ደግሞ ሰይጣን ነው፡፡ የእርሱ ፈቃድ በምንም ዓይነት መንገድ የክርስቶስ ስም እንዳይጠራ ማድረግ ነው፡፡ አቤቱ አምላኬ ስለምወዳቸው ስለእነዚህ በአመለካከታቸው  ገና ወተት ላይ ላሉት ማስተዋልን ስጣቸው፡፡ ፈቃድህን ተረድተው እንደተርብ ከመናደፍ እንዲመለሱ እርዳቸው፡፡ መስቀል ለእኔ መንግሥተ ሰማያት ማለት ነው ከጌታዬ ከአምላኬ ከአባቴ ከአፍቃሪዬ ከክርስቶስ ጋር የምኖርበት ቤቴ ነው፡፡
በመስቀሉ ለክርስቶስ ኢየሱስ አፍቃሪያን ሁለት ምግቦች ተሰጥተዋል፡፡ አንደኛው ፍቅር ነው፡፡ሁል ጊዜ ወደ መስቀሉ ስመለከት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ስለማፍቀሩ የተቀበለውን ጽኑ መከራ አስባለሁ፡፡እኛን ለማዳን ሲል የተቀበለውን መከራ ሳስብ ደግሞ ጥልቅ የሆነውን ፍቅሩን አስተውለዋለሁ፡፡ ስለእኛ መሞቱ ግድ ቢሆንም የተቀበለውን መከራ ሳስታውስ በከባድ ኃዘን ውስጥ እወድቃለሁ፡፡ ኃጢአቴም ትዝ እያለኝ የተዋለልኝን ውለታ ዘንግቼ እርሱን ጌታዬን በማሳዘኔ ቁጭት ሃዘን ይነግሥብኛል፡፡ በዚህም ምክንያት እኔ ከልጆቹ ልቆጠር የማይገባኝ ሲኦል ስለኃጢአቴ የምታንሰኝ እንደሆነች ሆና ትሰማኛለች፡፡ ኦ ፍቅርን እኮ ነው የበለደልኩት!!!


Monday, May 7, 2012

የአዳም እናትነት



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
29/08/2004
አምላኬ ሆይ አንተ ስለኢየሩሳሌም ጥፋት አዝነህ “ኢየሩሳሌም ኢየሩሳሌም ሆይ ነቢያትን የምትገድል ወደ እርሷ የተላኩትንም የምትወግር ዶሮ ጫጩቶቹዋን ከክንፎቹዋ በታች እንደምትሰበስብ ልጆችሽን እሰበስብ ዘንድ ስንት ጊዜ ወደድሁ አልወደዳችሁምም”(ማቴ.23፡37) ብለህ በተናገርከው ኃይለ ቃል   የአዳምን እናትነት ልብ አልኩኝ፡፡
ጌታችን አዳምን ከምድር አፈር አበጅቶ የሕይወት አስትንፋስን እፍ አለበት፤ በዚህም ምክንያት አምላኩን መሰለ፡፡ ከጎኑም አንዲት አጥንትን ወስዶ በእርሱ አርአያና አምሳል ሔዋንን በማበጀት በአካል እንድትገለጥ አደረጋት፡፡ ከዚህም በኋላ ከእነርሱ የሚገኙ ሁሉ እነርሱን እንዲመስሉ እነርሱ ያላቸውን ሕይወት ሕይወታቸው አድርገው እንዲኖሩ በእነርሱና በዘሮቻቸው የልጅ ልጆቻቸውን ሁሉ ፈጠረ፡፡ እንዲህ በመሆኑም የአዳም ቅድስና ለእነርሱ ሕያውነት፤ የእርሱ ውድቀት ለእነርሱ ውድቀት ሆነ እንጂ ልክ እንደ መላእክት አንዱ ቢወድቅ ሌላው ጸንቶ በመቆም የሚድን አልሆነም፡፡ ስለዚህም አዳም ወደቀ እኛም የእርሱ የውድቀቱ ተጋሪዎች ሆንን፡፡ እግዚአብሔር በረድኤት ከአዳም ሲለይ ከእኛም በረድኤት ተለየ፡፡ ምንም እንኳ የአዳምና የሔዋን ኃጢአት ተባባሪዎች ባንሆንም የውድቀታቸው ተጋሪዎች ሆንን፡፡ ምክንያቱም በአዳም አንድ ሰው ሆነን ተፈጥረናልና፡፡