Monday, October 21, 2013

በክርስትና ያለ እምነት እስከዚህ ድረስ ይረቃል


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
11/02/2006
 ክርስቲያን በክርስቶስ እንደሞተ ሊያምን ሕይወቱም ከክርስቶስ ጋር እንደተሰወረ ወይም ሕይወቱ ከሕያዋን ቅዱሳን ጋር አንድ እንደሆነ ሊያምን ይገባዋል፡፡ በክርስቶስ ያለው ሕያውነት በፈቃድ በሚሆን ሞት ማለትም ጥምቀት የመጣ ነው፡፡ በፈቃዳችን በእምነት ከክርስቶስ ጋር ሞተን የትንሣኤውም ተካፋይ በመሆን በክርስቶስ ሕያዋን ሆነን እንኖራለን፡፡ አሁን ያለን ሕይወት ከሕያዋን ጋር አንድ የሚያደረገን ሕይወት ነው፡፡ በሥጋ ሞት ሞትንም አልሞትንም በክርስቶስ በተነሣነው ትንሣኤ ሁሌም ለዘለዓለም ሕያዋን ሆነን እንኖራለን፡፡ ስለዚህ ለአንድ ክርስቲያን የሥጋ ሞት ከሕያዋን ጋር የሚያቆራርጠው ወይም እነርሱ በሥጋ ስለተለዩት ከእርሱ የሚለዩት አይደለም ይልቅ በክርስቶስ አንድ ቤተሰብ በመሆን የአንድ የእግዚአብሔር ልጆች ሆነው የሚኖሩበት ነው፡፡ ይህ በክርስቶስ ሞቼ ከክርስቶስ ጋር ተነሥቼለሁ አሁን ያለሁት ቅዱሳን በከተሙበት በሰማያዊ ሥፍራ ነው፡፡ እንዲያም ቢሆን በሥጋ ስላልሞትሁ በዚህ በሰማያዊ ሥፍራ ሆኜም ውጊያ አለብኝ በውጊያዬ ደግሞ ሰማያዊያን መላእክት እንደሚራዱኝ እንዲሁ በሰማያዊ ሥፍራ ፍጹም ዕረፍትን ያገኙ ቅዱሳን የእግዚአብሔርና የክርስቶስ ካህናት ሆነዋልና እድን ዘንድ በጸሎታቸው ይራዱኛል የሚለው እምነት ከክርስቶስ ጋር ሞቼ በትንሣኤው ሕይወት ሕያው ሆኜ እኖራለሁ ብሎ ማመንን በብርቱ የሚጠይቅ እምነት ነው፡፡

Wednesday, October 16, 2013

ምንኩስናና ትዳር የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች


05/02/2006
በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ


ክርስትና ለሰይጣን ይገዛ ከነበረ ዓለም ወጥቶ እርሱ የጽድቅ ጸሐይ የሆነው ክርስቶስ ብርሃን ሆኖት በቀን እንጂ በጨለማ የማንመላለስበት የቀን ልጅ ተሁኖ የሚኖርበት ሕይወት ነው፡፡ ክርስትና ከክርስቶስ ጋር ተሰቅለን ነፍስ በምትሰጠው ሕይወት ሳይሆን ለዘለዓለም አባ አባ ብለን የምንጠራበትን መንፈስ በሰጠን በመንፈስ ቅዱስ ሕያዋን ሆነን የምንኖርበት ሕይወት ነው፡፡ ስለዚህም ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር ራሳችንን ለጽድቅ ሥራ ያጨን ደናግላን ነን፡፡ አገባንም አላገባንም ለክርስቶስ የታጨን በመሆናችን ደናግላን ነን፡፡ ይህ ድንግልና የሚጠፋው ክርስቶስን ክደን በሰይጣን ሕያዋን ሆነን የኖርን ሰዓት ነው፡፡ቢሆንም ግን ይህም ቢሆን በንሥሐ የሚታደስ ድንግልና ነው፡፡ ጌታ ጠፍተን እንድንቀር የማይወድ ከኃጢአታችን ይልቅ መጥፋታችን የሚያሳዝነው በንስሐ በተመለስን ጊዜም በደስታ እጆቹን ዘርግቶ በፍቅር የሚቀበለን አምላክ ነው፡፡

Friday, August 16, 2013

የሙታን ትንሣኤና የጥምቀት ፍሬ እንዲህ ነው (1ቆሮ.15፡45-50)



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
10/12/2005 ዓ.ም
ቅዱስ ጳውሎስ “የሙታን ትንሣኤ እንዲህ ነው፡-” በማለት  ትንሣኤችንን ከለበስነው ሰማያዊ አካል ማለትም በጥምቀት ከለበስነው አዲስ ተፈጥሮ ጋር አዛምዶ ሂደቱን እንዲህ ይገልጥልናል፡፡ “በመበስበስ ይዘራል” ይህ አስቀድመን ስለለበስነው በዘር በሩካቤ ስላገኘነው ሰውነት ሲናገር ነው፡፡ ይህ አካል ሟችና በስባሽ አካል ነው፡፡ ስለዚህም “በመበስበስ ይዘራል” ያም ማለት ይሞታል፡፡ ይህም ስለትንሣኤችን ሊናገር እንደ መንደርደሪያ ያነሣው ነጥብ ነው፡፡ ሲቀጥል “ባለመበስበስ ይነሣል” ይላል፡፡ ይህ ቃል የሰውን ሁሉ ትንሣኤ ይናገራል እንጂ የክርስቲያኖችን ትንሣኤ ብቻ የሚናገር አይደለም፡፡ በትንሣኤ የሰው ዘር ሁሉ ለፍርድ ይነሣል፤ ዘለዓለማዊ ደስታን ወይም ዘለዓለማዊ ኩነኔን በኃጥአንና በጻድቃን ላይ በሚፈርደው በክርስቶስ የፍርድ ወንበር ፊት ቆሞ ይቀበላል፡፡(2ቆሮ.5፡10) ይህም አንዱ ለጽድቅ አንዱ ለኩነኔ መነሳቱን የሚገልጥ ነው፡፡
ቀጥሎ ግን በእውነት ክርስቲያን ለሆኑት ወገኖች የተሰጠው ትንሣኤ ምን እንደሚመስል ያስረዳል፡፡ ምክንያቱም በጥምቀት አዲሱን ሰው ብንለብሰውም ተመልሰን ለኃጢአት ባሮች ከሆንን በጥምቀት አዲሱን ሰው በመልበሳችን አንዳች ዋጋ እንደሌለን አስቀድሞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አስተምሮናልና “ወንድሞች ሆይ” ይለናል “ይህን ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ፡፡ አባቶቻችን ሁሉ ከደመና በታች ነበሩ” አለን፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ያላቸው የቆሮንቶስ ክርስቲያኖችን እንደሆነ አንባቢው ልብ ሊል ይገባዋል፡፡ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ከጣዖት አምልኮ ወደ እግዚአብሔር አምልኮ የመጡ ናቸው ወይም አሕዛብ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ለእነርሱ “አባቶቻችሁ ናቸው” ያላቸው እስራኤላዊያንን እንደሆነ አስተውሉ፡፡