Sunday, January 15, 2017

አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ስለ ጥንተ አብሶ

በቀጥታ የተወሰደ
08/05/2009


መቼም የአለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት መጽሐፍን  የቃላትን ትርጉም ሽቶ የማያነብ የለም ብዬ እገምታለሁ፡፡ ነገር ግን መግቢያቸው ከመርዘሙ የተነሣ ትግሥእት ኖሮት የሚያነብ ጥቂቱ ነው ብዬ አምናለሁ ከእኔ ጨምሮ ማለት ነው፡፡ አንድ ወቅት እንዲሁ አለፍ አለፍ ብዬ የመዝገበ ቃላቱን መግቢያ ስመለከት ይህን ጽሑፍ አገኘሁት፡፡ ዛሬ ደግሞ ደግሜ አነበብሁት ይህ ጽሑፋቸው ምናልባት በጥንተ አብሶ ዙሪያ ያለውን የቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ግልጽ ሳያደርግልን አይቀርም በሚል አንባቢ እንዲያነበው ስል እነሆ ብያለሁ፡፡

በእውነት ብፅዕት


ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
7/5/2009

ያቺ ቅድስት ብላቴና ንጉሥ እልፍኙ ያደርጋት ዘንድ ሳይፈጥራት ያወቃት፥ ከማኅፀን ሳይሠራት እናቱ ትሆን ዘንድ የነፍሷን ውበት ተመልክቶ የወዳዳት፥ ቤተ መቅደሱ በመሆን የእንስሳት መሥዋዕት የሚሠዋበትን የኦሪቱን ቤተ መቅድስ ልታሳልፍ የ"ቃል" ቤተ መቅድሱ ለመሆን ተመረጠች። በመንፈስ ቅዱስ የከበረች፥ አብ ልጁን ጸንሳ ትወልድ ዘንድ የሚያጸናት ፥ ራሱን ቤተመቅደስ ላለው ቃል ቤተ መቅድሱ ለመሆን የታጨች፥ ወላጅነትን ከአብ ጋር ለመጋራት የተመረጠች፥ መንፈሷ በመንፈስ ቅዱስ በሆነ ደስታ የተሞላ፥ ነፍሷ በአምላኳና በመድኅኒቷ ሐሴት የምታደርግ ፥ በሲኦል ላሉ ነፍሳት  በምድር ላሉ ሙታን የመዳናቸው ተስፋ የነበረችና ናፍቆታቸው የሆነች በእናቷ ሃና እጅ እርጅና ወደ ደቆሳት ቤተመቅድስ ገባች።

Friday, January 6, 2017

የዕብራውያንን መልእክት እንዲህ እንረዳው? መቅድም

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ቀን 28/04/2009)

ክብር ይግባውና ሥላሴ በፍቅር ሸንጎው ስለ ሰው ልጆች መዳን ምክርን መከረ፡፡ ሰው በድሎአል አሳዝኖናልም ቢሆንም አርዓያችን ነውና ፈጽመን ልንጥለው አይገባንም  አለ። በመቀጠል “አዳም ከእኛ እንደ አንዱ ይሆናል” ለጊዜው ግን ከእኛ ርቆ ይኖራል ብሎ ወሰነ፡፡ ምክራቸውንም እውን ለማድረግ ዘመን የማይቆጠርለት ሥላሴ ቀን ቆረጠ፡፡ በአርዓያውና በአምሳሉ የፈጠረውን የሰውን ልጅ ቤተሰብ ሊያደርግና ከወደቀበት ሊያነሣው እንዲሁም በእሪናው ሊያስቀምጠው ወልድ በፈቃዱ ሰው ሆነ፡፡
እርሱም ከአምላክነት እሪናው ሳይለይ ከቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ተገኘ፤ ሥጋና ነፍስ ነሥቶ ከጸጋ ተጓድሎ ደህይቶና ጎስቁሎ የነበረውን የሰውን ባሕርይ ገንዘቡ በማድረግ ሁሉን ወራሽ አደረገው፡፡ ከሥጋዌ በፊት የአብ የሆነ ሁሉ የወልድ ነበር የወልድ የሆነ ሁሉ የአብ ነበር፡፡ ይህ ሥጋ በመሆኑ የቀረ አልነበረም፡፡ ይልቁኑ የቃል የሆነ ሁሉ የሥጋ በመሆኑ ምክንያት ቃል ሥጋን ሁሉን ወራሽ አደረገው፡፡
በዚህ ግን ቃል ብቻ ሳይሆን አብም መንፈስ ቅዱስም ሥጋን ሁሉን ወራሽ አድርገውታል፡፡ አብ በማጽናት መንፈስ ቅዱስ በመክፈል ወልድ በመዋሐድ እኩል ተሳትፎ ነበራቸው፡፡ ስለዚህ ሥጋን የእግዚአብሔር ቃል የሆነውን ሁሉ ገንዘቡ እንዲያደርግ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ እኩል ሚና ነበራቸው፡፡  ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ አብን ርስት ሰጪ በማድረግ ስለ ክርስቶስ “ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን” ማለቱ፡፡