Tuesday, January 24, 2017

ፊደል ይገድላል መንፈስ ግን ያደናል



ዲ/ሽመልስ መርጊያ
16/05/2009

ጸሐፍት ፈሪሳውያን መጻሕፍትን በማወቅ የዘለዓለም ሕይወት የሚገኝ ይመስላቸው ነበረ፡፡ ነገር ግን ሕይወትን የሚሰጠው ወይም ሰውን ሕያው አድርጎ ሕያው የሆነውን ቃሉን እንዲረዳ የሚረዳው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ጸሐፊው መንፈስ ቅዱስ የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስ መረዳት የሚቻለው በመንፈስ እንጂ ስላነበቡት አይደለም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን ያነበበ ሁሉ መጽሐፍ ቅዱስን አውቆአል ማለት  አይቻልም፡፡ ምክንያቱም ከአእምሮ በላይ የሆኑ፤ ነገሮች ሳይፈጸሙ አስቀድሞ የሚያውቅ እርሱ እግዚአብሔር በመንፈሱ ያጻፈው ነውና፡፡ ስለዚህ ሊረዱዋቸው የሚቻለው በመንፈስ ቅዱስ ድጋፍ ነው፡፡ ስለዚህ መጻሕፍትን ለማስረዳት የተረዳነውን ለማብራራት የመንፈስ ቅዱስ ድጋፍ ብቻኛ መንገድ ነው፡፡ ፍጥረታዊ በሆነ አእምሮ መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳት መሞከር እንደ ጸሐፍት ፈሪሳውያን መሆን ማለት ነው፡፡ ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ ይቀድማል ቅዱሳት መጻሕፍት ይከተላሉ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰው መጽሐፍ ቅዱስን ይረዳል፡፡ 
ያለ መጽሐፍ ቅዱስ ድጋፍ በእርሱ አሳሳቢነት እንደ አበው ቅዱሳን(ከአዳም -ሙሴ) ወይም እንደ ሐዋርያቱ በጽድቅ ጎዳና ሊራመድ ይችላል ነገር ግን መንፈሱ ያላደረበት አይሁዳዊ ከሆነ ግን የግድ መጽሐፍ በሚለው ብቻ ሊራመድ ይገደዳል፡፡ ቢሆንም ግን ያለመንፈስ ቅዱስ ድጋፍ ስለሆነ ማንበቡ ብቻውን ወደ መዳን አያደርሰውም፡፡ ቃል ይገድላል መንፈስ ግን ሕይወትን ይሰጣል እንዲል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰው ግን ቅዱሳት መጻሕፍትን ባነበበ ቁጥር ሁሉ በቀላሉ በመንፈስ ቅዱሰ ገላጭነት ይረዳቸዋል፡:
 በእርግጥ በመጻሕፍት ብቻ ሕይወት የሚገኝ ለሚመስላቸው ወገኖች የመንፈስ ቅዱስን ድጋፍ ስለማያውቁ መንፈስ ቅዱስን ሊሰሙት ሊረዱትንም አይችሉም፡፡ ስለዚህ ክርስቶስን ሊያውቁት ሊረዱት አልቻሉም፡፡ ብዙ ጊዜ ሰዎችን የሚያሰናክለው ያለ መንፈሰ ቅዱስ ድጋፍ በአእምሮ ጠባያቸው ብቻ ተደግፈው መጻሕፍትን እንረዳ ባሉ ጊዜ ነው፡፡ ስለዚህ ስለ ክርሰቶስ ያላቸው ግንዛቤ እጅግ የተዘበራረቀ ይሆናል፡፡ ወይም በቀጥታ ቃሉን ይዘው ሰማያዊ የሆነውን እንደ አእምሮ ጠባያቸው በመረዳት ምድራዊ ያደርጉታል፡፡  መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰው ግን በመንፈስ የተጻፈውን ይረዳል፤ በመንፈስ ቅዱስ ምሪት ሁሉን ይተነትናል ሲያብራራም ለሕሊናችን፣ ለተፈጥሮአችን የሚስማማ በመሀኑ ነፍሳችን ትፈካለች ፡፡ ስለዚህ ከመጽሐፍ ቅዱስ መንፈስ ቅዱስ ይቀድማል፡፡ ኦርቶዶክስ እንዲህ ናት ይህም ማለት ከጥንት የነበረችው እስካሁንም ያለችው ለዘለዓለም ሕያዊት ሆና የምትኖረዋ ክርስትና ማለቴ ነው፡፡

Sunday, January 22, 2017

"ሥጋን ለበሰ" ማለት ትርጉሙና ምንጩ?


ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
14/05/2009
በአበው ሊቃውንት ዘንድ የቃል ሥጋ መሆን ወይም የሥጋ አምላክ መሆን ለማስረዳት ሲሉ “ሥጋ ለበሰ” የሚለውን ቃል መጠቀም የተለመደ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ “ለበሰ” የሚለው ቃል እንደ አገባቡ የራሱ የሆነ ትርጉም አለው፡፡ ልብስ ለበሰ፣ ኤፉዱን ለበሰ፤ ኃይልን ለበሰ ወዘተ የሚሉ ዐረፍተ ነገሮችን በተለይ በኦሪቱ በስፋት ተጽፎ እናገኘዋለን፡፡ ነገር ግን ይህን በምንረዳበት መንገድ ከታች ያሉትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች መረዳት አንችልም፡፡ ለምሳሌ፡- “እግዚአብሔርም ምድርን እነሆ ተበላሸች ሥጋን የለበሰ ሁሉ በምድር ላይ መንገዱን አበላሸቶ ነበርና”(ዘፍ.6፡12) የሚል ቃል አለ፡፡ በዚህ ሥፍራ “ሥጋን የለበሰ ሁሉ” ሲል ሥጋን እንደ ልብስ የለበሰ ማለት ሳይሆን “ሰው የሆነ ሁሉ” ማለቱ እንደሆነ ለሁሉ ግልጽ ነው፡፡

Tuesday, January 17, 2017

ፕሊሮማ

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
09/05/2009
ይህ ጽንሰ ሐሳብ ሰው ሁሉ በአዳም እንደሞተ በክርስቶስ ይድናል የሚለውን ነጥብ መሠረት ያደርጋል፡፡ በእርግጥ አንዳንዶች እንደ አዲስ ግኝት ቆጥረው ቢያራግቡትም ጽንሰ ሐሳቡ እንደ ሐሳብ መነሣት የጀመረው 2ኛው /ዘመን በአርጌንስ ወይም በኦሪግን ነው፡፡ አርጌንስ ወይም ኦሪግን ፍጥረት ሁሉ ይድናል ብሎ የተነሣው  በጊዜው በፍልስፍና ውስጥ ተተብትበው የነበሩትን ለመመለስ ሲል ነበር፡፡ በእርግጥ ሰውም ይሁን ሰይጣን ለመዳን ፈቃደኛ ከሆነ እግዚአብሔር ሊያድናቸው ይችላል ቢሆንም ግን የገዛ ፈቃዳቸው ገድቦአቸው ከመዳን ርቀው ተገኝተው ነው እንጂ እግዚአብሔር እነርሱን ለማዳን ፈቃዱ ሳይኖረው ቀርቶ አይደለም።
ለምሳሌ ቅዱስ ጳውሎስ ግሪካውያንን ወደ ክርስትና ለመመለስ ሲል  “የምታመልኩትን እየተመለከትሁ ሳልፍ። ለማይታወቅ አምላክ የሚል ጽሕፈት ያለበትን መሠዊያ ደግሞ አግኝቼአለሁና። እንግዲህ ይህን ሳታውቁ የምታመልኩትን እኔ እነግራችኋለሁ።”(የሐዋ.1723) ማለቱን ልብ እንላለን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ማለቱ ግሪካውያንን ለመመለስ ሲል እንጂ በአግባቡ ሳያውቁ የሚያመለኩት ክርስቶስን ነበር እያለ እንዳልሆነ ማንም ልብ ይለዋል፡፡ ነገር ግን እነርሱን ወደ ክርስትና ለማቅረብ እንደ መግቢያ በር ግን ተጠቅሞበታል፡፡ ይህ መንፈሳዊ ጥበብ ነው፡፡ ስለዚህም ሳታውቁ የምታመልኩትን እኔ ልንገራችሁ በማለት እነርሱን ወደ ክርስቶስ አምልኮ እንዳመጣቸው እንረዳለን፡፡ እንዲሁ በአርጌንስ ጊዜ ፍልስፍና ያለ ልክ ከፍ ከፍ ያለበት ጊዜ ስለነበረና እነርሱም የክርስቲያኖች አምላክ ጭካኝ ነው፤ አምላካቸው በአእምሮ ከእርሱ የሚያንሱትን በድለው ሲገኙ ሳይራራ ወደማይጠፋ ዘለዓለማዊ እሳት ይጨምራቸዋል የሚል አስተምህሮ አላቸው ብለው ክርስትናን ከመቀበል ተመልሰው ነበረና፡፡