Tuesday, May 2, 2017

የሕይወታችን ሁለቱ ጫፎች


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
25/08/2009

በሕይወታችን ጫፍና ጫፍ ያሉ ጊዜአትንና ተፈጥሮአዊ ባሕርያቸውን ሳስባቸው ግርም ድንቅ ይለኛል፡፡ መመሳሰላቸውንም ሳስብ ደግሞ ይበልጥ እደነቃለሁ፡፡ እነርሱም ሕፃንነትና አረጋዊነት ናቸው፡፡ ሁለቱም ከሌላ አካል አካላዊ ድጋፍን የሚሹ ናቸው፡፡ የሁለቱም ፆታ አገልግሎት አይሰጥም፡፡ አንዱ በተፈጥሮ ስላልተዘጋጀ ሌላኛው ግን ተፈጥሮ ራሷ ከአገልግሎት ስላወጣችው ነው፡፡ እናም ሁለቱም በመላእክት ሥርዓት የሚኖሩ ናቸው፡፡ ሁለቱም የእኛ ፈቃድ ሳይጠየቅ በአምላክ የሚፈጸሙ ናቸው፡፡ ነገር ግን አንዱ ወደዚህ ዓለም የሚያስገባ በር ሲሆን ሌላኛው ወደማታልፈው ዓለም የሚያሸጋግር መውጫ  ነው፡፡ ጎዳናቸው ግን አንድ ነው፡፡ አንተ አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ እንዲል ከምድር አፈር ከተበጀ አካል ተወልደን ወደ ቀደምት የአያታችን ማኅጸን ወደ ሆነች ምድር እንገባለን፡፡ ከእርሷም በትንሣኤ ተወልደን ለፍርድ በአምላክ ፊት እንቆማለን፡፡ በሥጋ ከወላጆቻችን ተወልደን በየሰከንዷ በሞት ጎዳና እንጓዛለን፡፡ አንዱ ይቀበላል ሌላኛው ይሸኛል፡፡ አንዱ በባሕርይው ያልተዳደፈ ንጹሕ ሲሆን ሌላኛው ግን ንጽሕናውና ቅድስናው እንደ ግብሩ ይወሰናል፡፡ ዕድሜችንን ሙሉ መልካምን በመሥራት ካሳለፍን በንጽሕናና በክብር ከሕፃንነት እንበልጣለን፡፡ አንዱ ለአዲስ ሕይወት የተዘጋጀ ሲሆን ብዙ ፈተናዎች ከፊቱ ይጠብቁታል፡፡ ሌላኛው ግን በዚህ ዓለም መኖርን አስረጅቷት የሰማያዊውን ሕይወት ጣዕም ማጣጣም የሚጀምርባት ሲሆን የኖረባትም ምድር እርሱን ከአገልግሎት ጡረታ የምታወጣበት ዕድሜ ነው፡፡ እግዚአብሔር ፈቅዶ ለእርጅና ከበቃን  የሞትን ጣዕም በእርጅናችን ማጣጣም እንጀምራለን፡፡ ሞት በአካላችን ሥራውን መሥራት ስለሚጀምር ጉልበታችን ይከዳናል፤ ዓይናችን ይፈዛል፤ ጆሮችን ይደነግዛል፤ አካላችን ይቀዘቅዛል፤ ጠጉራችን ይሸብታል ወይም ይመለጣል፤ ቆዳችን ከአጥንታችን ጋር ይጣጋል፤ ወዛችን ይረግፋል፤ መዓዛችን ይለወጣል፡፡  ያኔ መልካምን ሠርተን እንደሆነ አምላክ ቶሎ ወደ እርሱ እንዲወስደን እንለምነዋለን፡፡ ካልሆነ ግን በነፍስም በሥጋም ስቃያችን ይጨምራል፡፡ ወገኖቼ በእርጅና ሲኦልን በሚመስል ሕይወት ውስጥ ከመኖር ይጠብቀን፡፡  

Friday, April 14, 2017

የነፍስ ወግ

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
6/08/2009

ረቂቅ የሆነ እርሱ ፈጣሪዬ በእርሱ ፊት ምንም ግዙፍ ብሆን ሚስቴ ላደረጋት ከምድር አፈር ለፈጠራት ሥጋዬ በእርግጥም ረቂቅ ነኝ፡፡ እርሱ የፈጠረኝ አምላክ በእርሱ አርአያና አምሳል የፈጠረኝ ቢሆንም እንደርሱ ረቂቅ ስለሆንኹ ረቂቃኑ መላእክትም ግዙፋኑ ፍጥረታትም የእርሱን አርአያ በግዘፍ እንዲያዩ አምለክ ሥጋ ሚስቴን ግዙፍ አድርጎ ፈጠራት፡፡
 ከመላእክት እኔ የምለየው ከሥጋ ጋር አንድ አካል መሆን ስለሚቻለኝ ነው፡፡ በሌላ ተፈጥሮዬ ግን ከእነርሱ ጋር አንድ ነኝ፡፡ ቢሆንም ለእኔ ከውድቀት በፊት የነበረው የሥጋ ተፈጥሮ በእጅጉ ይስማማኝ ነበር፡፡ ምክንያቱም በገነት ለሥጋ የተሰጡ መብላት ሥጋን በሕይወት እንድትቆይ ምንም ዓይነት ሚና የላቸውምና ሥጋን በሕይወት ለማቆየት ስል ምንም ድካም የለብኝም ነበርና፡፡ ከውድቀት በኋላ ግን ከመላእክት ጉባኤ በልዩ ተፈጥሮ ሆኜ የአምላኬን ፍቅር እየተመገብሁ ከምኖርበት መኖሪያዬ ገነት በራሴው ጥፋት የክፋት ምክንያት የሆነውን ሞትን በሥጋዬ ላይ ሹሜ፥ ፍቅርን አጥፍቼ ፥ ፍርሃትን አንግሼ ከመላእክት ጉባኤ ተለየሁ፡፡

Sunday, March 26, 2017

ምጽአቱ ለክርስቶስ


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
17/07/2009


ወዮ ይህች ከእውነተኛ ጌታ የወጣች ትምህርት እንዴት ታስፈራለች ? እርሱ  ስለትንሣኤ ሕይወታችን በዐሥሩ ደናግላን መስሎ አስተማረን እንዲህም አለን፥-"በዚያን ጊዜ" ያላት ያችን የምታስፈራዋን የምጽአቱን ቀን ነው።  በዚያን ጊዜ መንግሥተ ሰማያት መብራታቸውን ይዘው ሙሽራውን ሊቀበሉ የወጡ አሥር ቆነጃጅትን ትመስላለች" አለን። በአሥሩ ደናግላን የተመሰልነው እኛ በጥምቀት ለክርስቶስ የታጭነው ክርስቲያኖችን ነን። ስለሆነም ጌታችን ክርስቲያን መሆናችን ብቻ እንደማያድነን እምነትን ከምግባር፥ እምነትን ከፍቅር ጋር፥ እምነትን ከጦም ከጸሎት ከስግደት ከምጽዋት ጋር አብረን አስተባብረን ይዘን የብርሃን መላእክትን መስለን ራሳችንን ከኃጢአት ጠብቀን የጌታን መምጣት በናፍቆት እንጠብቅ ዘንድ እንዲገባን ሊያስተምረን እንዲህ አለን።