Friday, December 1, 2017

የትርምት ሕይወት እንደ ቅዱስ ኤፍሬም አስተምህሮ ካለፈው የቀጠለስለጻፋቸው መጻሕፍት


ቀን23/03/2010
በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን የታሪክ ምሁራን ቅዱስ ኤፍሬም የተነሣበት ዘመን ኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ በስፋት የበለጸገበት ዘመን ነበር ይላሉ፡፡
በቅዱስ ኤፍሬም ሥነ ጽሑፍ ላይ ተጽዕኖአቸውን ያሳደሩ የሥነ ጽሑፍ ስልቶች እነዚህ ናቸው፡፡  
ሥዕላዊ የአገላለጽ ስልት የሚባለው የጥንት ሶርያውያን ክርስቲያኖች የአጻጻፍ ስልት(Mesopotamian mystery of Symbolism)
የአይሁድ የሥነ ጽሑፍ ስልት
የግሪክ ፍልስፍና  ናቸው፡፡
ስለዚህ አንድ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ምሁር ቅዱስ ኤፍሬምን የሜሶፖቶሚያ፣ የአይሁድ እንዲሁም የግሪክ ሥነ ጽሑፍ መገናኛ ይለዋል፡፡ እነዚህ በአንድነት እንደፈለገ የሚጠቀም ቅዱስ አባት ማግኘት ከባድ ነው፡፡ ለቅዱስ ኤፍሬም ግን ተችሎት ነበር፡፡
የቅዱስ ኤፍሬም ብዙዎቹ ሥራዎች በመዝሙር መልክ የተዘጋጁ ቅኔአዊ ድርሰቶች ሲሆኑ ይህም የሜሶፖቶሚያው ሥዕላዊ የጽሑፍ ስልትን አብዝቶ እንደሚጠቀም ያሳያል፡፡
የቅዱስ ኤፍሬምን ሥራዎችን ለሦስት ልንከፍላቸው እንችላለን፡
የደረሳቸው መዝሙራት
የጌታችን መዋዕለ ሥጋዌ ላይ ያተኮሩ
ስለጥምቀት ክብረ በዓል የሚያወሱ
ስለዕንቍ ሰባት መዝሙራት(በእምነት ላይ የሚያተኩሩ ናቸው)
ስብከቶች
ስለ ሥጋዌ
ተግሣጽና ስለንስሐ  
ስለ ኃጢአተኛዋ ሴት
ትርጓሜያት
ዘፍጥረት አንድምታ
ዘጸአት አንድምታ
ወንጌላት አንድምታ(አንድ ወጥ ሆኖ 170 ዓ.ም በታትያን የተዘጋጀ)
አንዳንዶች የሐዋርያት ሥራንና መልእክታትን እንደተረጎመ ይናገራሉ፡፡ ግን ማግኘት አልተቻለም፡፡ አንድ በቅዱስ ኤፍሬም ሥራ ላይ ጥናት ያደረገ ሰባስቲያን ብሮክ የሚባል ጸሐፊ  የቅዱስ ኤፍሬም ሥራዎች የሚላቸው አሉ፡፡ እነርሱም፡-
ወደ ፖብሊየስ የተላከ ደብዳቤ (ስለመጨረሻው ፍርድ)
ስለኒቆሞዲያ ስለመሬት መንቀጥቀጥ የሚያወሳ ጽሑፉ ይገኙበታል፡፡
ግሪክ ኤፍሬም
ግሪክ ኤፍሬም የሚባሉ የኤፍሬም አሻራዎች ያረፉባቸው ግን በሶርያ ሊቃውንት ዘንድ ተቀባይነት የሌላቸው ጽሑፎች ናቸው፡፡ እነዚህ ሥራዎች የቅዱስ ኤፍሬም አይደሉም ወይም የእርሱ አሻራዎች የለባቸውም ማለት ግን እጅግ አስቸገሪ ነው፡፡
እነዚህም፡-
በእንተ ብፁዓን(ሃምሳ አምስት ምዕራፎች አሉት)
የብልጽግና ግምጃ ቤት
ስለ ግብጽ መነኩሳት
ስለ ጦም መዝሙር
በአካለ ሥጋ ስለሌሉ ቅዱሳን አባቶች
ስለ ፍቅር
ማኒን ተቃውሞ የጻፈው ጽሑፍ
መርቂያንን ተቃውሞ የደረሰው ድርሰት ይገኙበታል፡፡
በአጠቃላይ ቅዱስ ኤፍሬም ከዐራት መቶ በላይ መዝሙራትን የደረሰ ሲሆን ጥቂቶቹ ጠፍተዋል፡፡ የቅዱስ ኤፍሬም ሥራዎች ለትርጓሜ እጅግ አስቸጋሪዎች ናቸው፡፡ አስቸጋሪ ያደረጋቸው የጽሑፍ አወቃቀሩ የተወሳሰበ በመሆኑና በቃላት ላይ እጅግ ስለሚራቀቅ እንዲሁም ሥዕላዊ ገለጻዎች ስለሚበዙበት ነው፡፡ ስለዚህም የቅዱስ ኤፍሬምን መልእክት ለመረዳት ጥልቅ የሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ ዕውቀትና ሕይወቱ እንዲሁም ጥናት ይፈልጋል፡፡
ነገር ግን ጽሐፎቹ ወደ አርመን፣ ቅብጥ(ኮፕት)፣ ግሪክ፣ እንዲሁም ወደ ልዩ ልዩ ቋንቋዎች ተመልሶአል፡፡
ምዕራፍ ሁለት
የትርምት ሕይወት
የትርምት ሕይወት (Asceticism) ማለት ራስን ማረቅ መግዛት የሚለማመዱበት ሕይወት ማለት ነው፡፡ የትርምት ሕይወት በክርስቲያናዊ ሕይወታችን አንዱ ክፍል ሲሆን ማንኛውም ክርስቲያን ሊያልፍበት የሚገባ ሕይወት ነው፡፡ ምክንያቱም ክርስቲያን በሕይወቱ ዘመን ሁሉ እርሱን ሊፈትን የሚተጋ ጠላት አለበትና፡፡ ስለዚህ የዲያብሎስን ውጊያ ድል ለመንሣት አንድ ክርስቲያን የጽድቅን ጡሩር ሊለብስ ወይም የጽድቅን ሕይወት ልማድ ሊያደርግ ግድ ነው፡፡
ለዚህ አብነታችን ራሱ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እርሱ በዕደ ዮሐንስ ከተጠመቀ በኋላ ቀጥታ መንፈሰ ቅዱስ ወደ ምድረ በዳም ነበር የወሰደው፡፡ በዚያም ዲያብሎስን እንዴት እንዋጋው ዘንድ እንዲገባን አስተማረን፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህን የመጽሐፍ ክፍል ሲተረጉም አንድ ክርስቲያን በሕይወት ዘመኑ እንደ አዳም እንደ ኢዮብ በዲያብሎስ ይፈተናል፤ ምክንያቱም ሲጠመቅ የእግዚአብሔር ልጅ ሰለሚሆን ነው፡፡ አዳምን ከገነት እንዳስወጣው እንዲሁ እኛንም በክርስቶስ ካገኘነው የልጅነት ሥልጣን ሊያወጣን ዘወትር ይተጋል ብሎ ያስተምራል፡፡ እውነቱም ይህ ነው፡፡ ለክርስቲያን ከነፍስ የሆነ መታዘዝ እንዲኖረው ሰው በመሆን የሰውን ባሕርይ ያከበረውን የጌታችንን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትእዛዝ ሊያከብር ግድ አለበት፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር ቃል በሥጋና በደም በመካፈል የእኛ ዘመድ ሆኖናልና፡፡

የትርምት ሕይወት በቅዱስ ኤፍሬም

ቀን 23/03/2010
በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
መቅድም
ቅዱስ ኤፍሬም በጊዜው ገናናና ጥንታዊ በሆነች ንጽቢን 306-373 ዓ.ም ድረስ የኖረ ሲሆን፤ የሕይወት ዘመኑን ሁሉ በትርምት ሕይወት ያሳለፈ በትርምት ሕይወት ላይም ልዩ የሆነ አስተምህሮ ያለው ቅዱስ አባት ነው፡፡ እንደ ቅዱስ ኤፍሬም የትርምት ሕይወት የብሕትና ሕይወትን ለሚመሩ ብቻ የተሰጠ ሕይወት ሳይሆን ማንኛውም ክርስቲያን ሊኖርበት የሚገባ የሕይወት መንገድ ነው፡፡ ስለ ትርምት ሕይወት ሌሎች የሶርያ አባቶች አስተምረዋል የቅዱስ ኤፍሬም ግን ልዩና ጥልቅ ነው፡፡
በትርምት ሕይወት ላይ የሶርያ ቅዱሳን አባቶችን አስተምህሮ ባነበብሁ ሰዓት እጅግ ከመገረም በላይ እኛ ሕይወት እንዲሆንም ተመኘሁ፡፡ ምክንያት የእነርሱ የትርምት ሕይወት አስተምህሮ ከሥጋዊ ድንግልና ላይ ሳይሆን ውስጣዊ ድንግልና ላይ የተመሠረተ በመሆኑ ነበር፡፡ እንደነርሱ አስተምህሮ አንድ ሰው ራሱን ለእግዚአብሔር ፈቃድና ሕግ ካስገዛና አምላኩ ከመሠለ እርሱ  በእርግጥ ድንግል ነው፡፡ የሥጋ ድንግልና ለእነርሱ ከቁምነገር ውስጥ የሚገባ አይደለም በተለይ ለቅዱስ ኤፍሬም፡፡
ይህን ምልከታቸውን በአመክንዮነ መሠረታችንን መጽሐፍ ቅዱስ አድርገን ስንመለከተው ተገቢ እንደሆነም እናረጋግጣለን፡፡ ውስጣዊ ወይም የነፍስ ድንግልናችንን ጠብቀን ከተገኘን የሥጋ ድንግልናችንን መጠበቅ ይቻለናል፡፡ ጌታችንም ስለ ውስጣዊ ወይም የነፍስ ድንግልና ሲያስተምርም “ አታመንዝር እንደ ተባለ ሰምታችኋል እኔ ግን እላችኋለሁ ወደ ሴት ያየ ሁሉ የተመኛትም ያን ጊዜ በልቡ ከእርስዋ ጋ አመነዝሮአል፡፡”(ማቴ.5፡27) ብሎ አስተምሮናል፡፡ ስለዚህም አንድ ሰው ውስጣዊ ድንግልናውን ከኃጢአት ከጠበቀ ድንግል ነው፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው ሥጋዊ ድንግልናውን ጠብቶ በልቡ ቢያመነዝር ምንም የሥጋ ድንግልና ቢኖረውም ድንግልናውን እንዳጠፋ ይቆጠርበታል፡፡

Monday, October 30, 2017

ጌታ ይባርክህ ማለት ለማን ነው?

በዲ/ ሽመልስ መርጊያ
21/02/2010


የሁሉ ፈጣሪ የሆነው የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ፈቃድ ይህ ነው፡- በእውነት መዳንን ለሚሻ ወገን እንደ ኦሪቱ ጥላውን ሳይሆን ወይም አይሁድ በስደት ሳሉ በሙክራባቸው እንደሚፈጽሙት ዓይነት አምልኮ ሳይሆን በእውነት በእርሱ በክርስቶስ በጎውን ለማድረግ ተፈጥሮ፣ በእርሱ እረኝነት ሥር ሆኖ፣ ግልገል ጠቦት በግ ተሰኝቶ፣ ሰማያዊ ሥፍራ በተባለችው መንግሥቱ ውስጥ በእርሱ መለኮታዊ ብርሃን የቀን ልጅ ተብሎ ከጸጋው እየተመገበ እንዲኖር ነው ፈቃዱ፡፡
ይህች ዓለም ደግሞ ኢአማኒያን ዓሣትን ማጥመጃ ባሕር፤ ሰማያዊ ንግድን ነግደው የሚያተርፉባት ገበያ፣ በእግዚአብሔር እርሻ ውስጥ ንጹሕ ዘርን ዘርተው ሰላሣ ስልሳ መቶ ፍሬ የሚያፈሩባት ምድር ናት፡፡ ሁላችንም ኅብረታችን ከአንዱ እግዚአብሔር ጋር ነው ፍላጎታችንና መፈለጋችን ፈቃዳችንም እርሱ ነው፡፡ እምነት ከእግዚአብሔር እንጂ ከሰው ጉድፍ ጋር ኅብረት የለውም፡፡
ነገር ግን  የገነትን ጣዕም ያስረሱንን አዳምንና ሔዋንን ያሳተ ሰይጣን ከዚህች ረቂቅና ሰማያዊ ሥፍራ እኛን ለማስወጣን ይደክማል፡፡ ይህ የሚጠበቅ ነውና ጌታችን እኛን በሁሉ መስሎ ዲያብሎስን ድል በመንሣት ድል መንሣትን ለእኛ ሰጠን፡፡ የሚያሳዝነው ግን በምድር ያሉ ሁሉ የእርሱ ሲሆኑ እርሱ ቸሩ ፈጣሪ ለሰዎች ሲሰጣቸው ሰዎች ደግሞ የሰጣቸውን መልሰው ለዲያብሎስ በመስጠት ምንም ሳይኖረው ዲያብሎስን የዚህ ዓለም ገዢ ማድረጋቸው ነው፡፡ እርሱ ረቀቅ መንፈስ ነው፡፡ ምድር ደግሞ በዋነኝነት ለሰዎች የተሰጠች ናት፡፡ ምድር ለእኛና ለምድር ፍጥረታት የሚስማማ ተፈጥሮ እንጂ ለዲያብሎስ የሚስማማ ተፈጥሮ የላትም፡፡ ከምድር ፍሬ ዲያብሎስ ለመኖር ሲል አይበላም አይጠጣም አየሩም አያስፈልገውም፡፡ ድካምም የለበትም ዕረፍትም አያሰፈልገውም፡፡ ታዲያ ምን እንዲሆነው ነው የምድርን ገዢነት ለእርሱ የሰጡት?
ይበልጡኑ ግን ሰዎች በስሜ ይመጣሉ ብዙዎችንም ያስታሉ እንዲል ጻድቃን መስለው የዲያብሎስ ባሪያዎች መሆናቸው ነው የሚያሳዝነው፡፡ ጌታ ብለው የሚሰብኩን ፍጡር ስለሆነው ወደ ፊት ስለሚመጣው እኔ እግዚአብሔር ነኝ ስለሚለው ነው፡፡ ይህን ከፍሬአቸው ታውቃላችሁ፡፡ በዚህ ዘመን ለሃሳዊው መሲህ ነቢያትና መንገድ ጠራጊዎች የሆኑ ምድሪቱን ሞልተዋታል፡፡ ሁሉም ጌታ ኢየሱስ ስላለ እውነተኛውን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን እየጠራ በእርሱም ስም እየባረከ አይደለም፡፡ ሰይጣንም እንዲሁ ያደርጋል የእርሱ ብራኬ ታዲያ ምን ያደርግልናል? በዚህ በምናባቸው በተፈጠረው ኢየሱስ ስም ወይም በሃሳዊው መሲህ ስም ቢባርኩንም ቢረግሙንም ያው አንድ ነው፡፡ ሁለቱም ለእኛ የማይጠቅምም የማይጎዳም ነው፡፡ በእኛ ላይ አንዳች ስልጣን የለውምና፡፡ ይልቁኑ እኛ በእርሱ ላይ ስልጣን አለን፡፡
የድንግል ልጅ ባልሆነው ኢየሱስ ስም መባረክ ማለት በእርግጥ እርግማን ነው፡፡ ርግማኑ ግን በራሳቸው ላይ እንጂ በእኛ ላይ አይደለም በጣዖት ስም እየባረኩና እየረገሙ ናቸውና፡፡ ለምን ብትሉኝ አንደኛ የጌታችንን ስም ለፍጡር ያውም ለእርሱ ተቃዋሚ በመስጠታቸው ነው፡፡ ሁለተኛው ለዚህ ሃሳዊ መሲህ ልባቸውም አንደበታቸውም መገለገያ መሣሪያ ማድጋቸው ነው፡፡ በሦስተኛነት ደግሞ ጻደቅ መስለው ሌሎችን በመሸንገላቸውና ወደ ጥፋት በመጣላቸው ነው፡፡ እንዲያም ሆኖ ደግሞ የድንግል ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስን ከመልበስ፣ ከመመገብ፣ ከመጠጣት፣ በእርሱ ውስጥ ከመኖር በላይ ምን የተሻለ መባረክ አለና ነው ጌታ ይባርክህ የሚሉን? ነገር ግን በድንግል ማርያም ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ብትባርኩን እሰማችሁ ይሆናል፡፡ እንዲያም ቢሆን ግን በበልዓም ሥፍራ ሆናችሁ ስለሆነ ለእናንተ በእጅጉ አዝናለሁ፡፡
በኋለኞቹ ዘመናት በስሜ ይመጣሉ የተባሉ እነዚያ ሃሳውያን የሰይጣን ሎሌዎች ለሰው ልጆችም ሆነ ለራሳቸው እንደ አባታቸው ዲያብሎስ ጭላጭ ፍቅር የላቸውም፡፡ ግን እኛ እነርሱ ለዲያብሎስ መሳሪያ በመሆናቸው ብናዝንም እንድንጠላቸው አልታዘዝንም፤ ጠላትህን ውደድ ማለት እንዲህ ነውና፡፡ እነርሱ በዲያብሎስ ታውረው ይጠሉናል እኛ ግን እንዲሁ እንወዳቸው ዘንድ ታዘናል፡፡ ሰይጣንንም ቢሆን በእግዚአብሔር ፍጥረትነቱ አንጠላውም፡፡ ነገር ግን ተግባሩን እንጠላለን፡፡
እርሱ የፍቅር ጠላት ነውና ፍቅር የቀዘቀዘው እርሱ የጥል አባት ስለሆነ መለያየትን በሰዎች ላይ በመዝራቱ ነው፡፡ ጌታችንም “አባታችን ሆይ በሰማይ የምትኖር ስምህ ይቀደስ መንግሥት ትምጣ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁን የእለት እንጀራችንን ስጠን ዛሬ በደላችንን ይቅር በለን እኛ የበደሉንን ይቅር እንደምንል” እያልን ለራሳችን ብቻ ሳይሆን ለሰው ልጆች ሁሉ እንድንጸልይ አዞናል፡፡ ይህ ጸሎት ልመናም ምልጃም ነው፡፡ ጸሎቱ፣ ምልጃውና ልመናው በምድር ላሉ ሁሉ ነው፡፡ “ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁን” እንዲል፡፡
“የሚጠሉዋችሁን ብትጠሉ አሕዛብም ይኸንኑ ያደርጋሉና ምን ዋጋ አላችሁ?” እንዳለ ጌታችን መንግሥቱም በፍቅር የምትገለጥ ናት፡፡ እርስ በእርሳችሁ ብትዋደዱ የእኔ ደቀ መዛሙርት እንደሆናችሁ ሰው ሁሉ ያውቃል ይለናል፡፡ ግን እርስ በእርስ ብትነካከሱ የክርስቶስ አይደላችሁም፡፡ የክርስቶስ መንግሥት ውስጥ ፍቅር አለ፡፡
ቅዱስ ጳውሎስ “አንድ እግዚአብሔር፣ አንድ ጌታ ፣አንዲት ሃይማኖት፣ አንዲት ጥምቀት፣ አንዲት ቤተ ክርስቲያን ብሎ በአንድ አካል ያሉ እርስ በእርስ ፍጹም እንዲዋሐዱ ማድረጉ ስለምን ይመስላችኋል? እንዲህ አድርጎ ጌታችን እኛን በአዲስ ተፈጥሮ መፍጠሩ አምላክ መለያየትን በሚዘሩና ፍቅርን በሚያጠፉ ወገኖች ደስ እንደማይሰኝ ያሳየናል፡፡ በመስቀሉ አንድ ሊያደርገን ስለእኛ በመስቀል ላይ ዋለ፡፡ በስቅለቱም እኛን ወደ ላይ ወደ ሰማይ ሳበን ከቅዱሳን መላእክትና ከቅዱሳን ነፍሳት ጉባኤ ደመረን፡፡ ምድር ሰማይ ሆነች ሰማያውያንም በምድር በክርስቶስ ካሉ ጋር ኅብረትን ፈጠሩ፡፡ ይህ የሆነው ስለ ፍቅር ነው፡፡ እናም ዘመዴ ጌታ ያደረግኸውን ሳታውቅና ሳትለይ ጌታ ይባርክህ አትበለን፡፡ እኛ በእርሱ ያጣነው የጎለብን አንዳች ነገር የለምና፡፡