Wednesday, August 2, 2017

የነፍስ ወግ አምስተኛ ክፍል ስለ ሥነ ተፈጥሮዬ


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
27/11/2009

እግዚአብሔር እኔ ነፍስን ልክ እንደ አዳምና ሔዋን ከእኔ ጋር አንድ አድርጎ የፈጠራትን ግዙፏን ሥጋዬን እንድረዳት አድርጎ ፈጠረኝ። ስለዚህ አምላኬ እርሷን እንደሚያውቃት መጠን አይሁን እንጂ ሥጋዬን አውቃታለሁ፡፡ ምድርን በእርሷ ላይና ውስጥ ያሉትን እንደማጥናት እንዲሁ ግዙፋን ሥጋዬን በማጥናት ሁል ጊዜ አዳዲስ የሆኑ ነገሮችን ከእርሷ እያወቅሁ እኖራለው፡፡ ለዕውቀቱ ፍጻሜ የለውም፤ ብቻ እርሷን ለማወቅ ተሰጥቶኛልና ስለእርሷ ማንነት መናገር ብዙም አይቸግረኝም፡፡ የሚደንቀኝ ግን ስለ ራሴን መርምሬ ለማወቅ አለመቻሌ ነው፡፡ ረቂቅ መንፈስ መሆኔን አውቃለሁ ነገር ግን አይቼ ዳስሼ አረጋግጬ አይደለም፡፡ መዓዛዬን፣ ቁመቴን፣ ውፍረቴን፣ ቅጥነቴን ገጽታዬን ጭምር አላውቀውም፡፡ በአጠቃላይ መንፈስ መሆኔን እንጂ ለሌላው ማንነቴ ባይተዋር ነኝ፡፡ የሚደንቀው ግን መላእክት እርሷን ማወቃቸው ነው፡፡

Tuesday, July 11, 2017

አረጋዊው ማን ነው?

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
4/11/2009
መቼም ስለ ዕድሜ ሲነገር ቆጠራው ከጽንሰት ከተጀመረ እንደ ጻድቁ ኢዮብከሴት የተወለደ ሰው የሕይወቱ ዘመን ጥቂት ቀን ነው፥ መከራም ይሞላዋል”(ኢዮ.141) ማለታችን ግድ ነው፡፡ ከጽንሰት የምንጀምራት ዕድሜአችን እንደ ጠዋት ጤዛ ወይም እንደ ሳር አበባ ናት፡፡ ባንድ ቀን ለምልማ በአንድ ቀን የምትረግፍ አበባ ማለት ይህቺ ምድራዊዋ ዘመናችን ናት፡፡ ቢሆንም ዋጋ ያላትም ይህቺው ዕድሜአችን ናት፡፡ በዚህች ዕድሜአችን በሰውነት ሕዋሳቶቻችን ሁሉ መልካምን ካልሠራንባቸው ዕዳዋ ዘለዓለማዊ ሆኖ ይሠፈርብናል፡፡ ከሠራን ደግሞ የተጠቀጠቀና የተጨቆነ ብድራትን ከአምላክ ዘንድ እናገኝባታለን፡፡ ግን ደግሞ ዕድሜአችንን በአምላክ ሕሊና ከመታሰባችን ጊዜ አንስቶ እንደ ንጉሥ ዳዊትአቤቱያልተሠራ አካሌን ዓይኖችህ አዩኝ የተፈጠሩ ቀኖቼ ሁሉ አን ስንኳ ሳይኖር በመጽሐፍህ ተጻፉ”(መዝ.13816) ብለን የቆጠርን እንደሆነ ዕድሜአችን የትናለሌ ሊሆን ነው፡፡ ከመቼ ጀምሮ በአምላክ ሕሊና እንደታሰብን በጭራሽ አናውቀውም ግን ደግሞ አምላክ እንደ ሰው አያስብምና መነሻ አለው ማለት አይቻለንም፡፡ እርሱ ያሰበው ከዘለዓለም ያሰበው ነው፤ እንዲያስብ ምክንያቶች አያስፈልጉትም፡፡ የማያውቀው ወደፊት የሚያውቀው ነገር የለውም፡፡ ስለዚህ ዕድሜአችንን በእግዚአብሔር ሕሊና ከመታሰባችን አንስቶ ከቆጠርነው ሳንወለድም በፊት አረጋውያን ነን ምክንያቱም ሳይሠራን በሕሊናው ነበርን ሳንፈጠርም ቀኖቻቸችን በእርሱ ሕሊና የታወቁ ናቸውና፡፡
አደራ ግን ይህ ቃል ስለ ዳዊት ብቻ የተነገረ ነው እንዳትሉኝ ምክንያቱም አምላክ ሳያስበው የሚፈጥረው ነገር የለምና፡፡ አይደለም እርሱ እኛ እንኳ ያላሰብነውን አንተገብርም፡፡ በሕሊናችን የጨረስነውን በተግባር እንፈጽመዋለን፡፡ ስለዚህ ቃሉ ያለጥርጥር ለዳዊት ብቻ የሚሠራ ሳይሆን ለእኛም ይሠራል፡፡ እንዲህ ከሆነ ታዲያ ዕድሜአችን ስንት ነው? እንጃ እርሱ እግዚአብሔር ያውቀዋል እኛ ልናውቅ የምንችለው ቢኖር በሥጋ ተጸንሰን በዚህ ምድር የተመላለስንባትን ዕድሜ ብቻ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ዕድሜ የለም ከዚያም በኋላ በትንሣኤ ዕድሜ አይኖርም፡፡ ከእነዚህ አንጻር በሥጋ የምንኖርባት ይህቺ ዕድሜ ስትሰላ እንደ ጠዋት ጤዛ ጠዋት ታይታ ፀሐይ ሲተኩስ የምትጠፋ ወይም እንደ ምድር አበባ በአንድ ቀን አብባ በአንድ ቀን የምትከስም እንደሆነች እንረዳለን፡፡

Sunday, June 11, 2017

የነፍስ ወግ (በእንተ ደናግላን)


እንደ ጢሞቴዎስ ከልጅነት ጀምሮ ከቅዱሳን መጻሕፍትና ከመንፈስ ቅዱስ እንዲሁም ከትርምት ሕይወት ስለእግዚአብሔር የተማረ፤ የልቡናውን ደጅ በመዝጋት ከሕግ መምህር ትምህርቱን የቀዳ ክርስቲያን ለእርሱ ከትዳር ሕይወት ይልቅ የድንግልና ሕይወት እንዴት የተመረጠ ሕይወት አይሆነው? ይህ ሰው ማዕረጉ ከመላእክት ወገን ነውና የሥጋ ፍትወት የራቀለት በትንሣኤ ሕይወት የሚኖር እግዚአብሔር ሳይመርጥ ኃጥኡንም ጻድቁንም እንዲወድ ሁሉን የሚወድ በአንዲት ብላቴና ፍቅር ታሥሮ እርሱዋን አስቀድሞ ሌላውን አስከትሎ መውደድ የማይቻለው፣ እንደ አምላኩ ሁሉን አስተካክሎ የሚወድ በትዳር ውስጥ ያሉቱ ጥንዶች በትንሣኤ የሚያገኙት ሙሉዕ የሆነ ፍቅር አግኝቶ የሚኖር ሰው ነው፡፡